ከ100 ሺህ ብር በላይ አሮጌውን የብር ኖት የመቀየሪያ ጊዜ ጥቅምት 6 ቀን 2013 ዓ.ም ይጠናቀቃል
አዲስ አበባ ፣መስከረም 25 ፣2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ከ100 ሺህ እስከ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር አሮጌውን የብር ኖት በእጃቸው የያዙ አካላት እስከ ጥቅምት 6 ቀን 2013 ዓ.ም በአዲሱ የብር ኖት እንዲቀይሩ ብሄራዊ ባንክ አሳሰበ።
አሮጌውን የብር ኖት በአዲሱ የብር ኖት ለመቀየር መንግስት የ90 ቀናት የጊዜ ገደብ ማስቀመጡ የሚታወስ ሲሆን ከ100 ሺህ እስከ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር አሮጌ የብር ኖት ለመቀየር የተቀመጠው የጊዜ ገደብ 30 ቀናት መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
አሮጌውን በአዲሱ የብር ኖት የመቀየር ስራው መስከረም 6 ቀን 2013 ዓ.ም የተጀመረ ሲሆን ከ100 ሺህ እስከ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር አሮጌውን የብር ኖት የመቀሪያ ጊዜም ጥቅምት 6 ቀን 2013 ዓ.ም ተብሏል።
በመሆኑም ህብረተሰቡ በመንግስትም ሆነ በግል ባንኮች በእጃቸው የሚገኘውን አሮጌውን የብር ኖት በተሰጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ እንዲቀይሩ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል።