በክልሉ የተጀመሩ መሠረተ-ልማቶች ግንባታን በዚህ ዓመት መጨረሻ ለማጠናቀቅ እየተሠራ ነው
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 12፣2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ከ1 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር በሚልቅ ወጪ የተጀመሩ መሠረተ-ልማቶች ግንባታን በዚህ ዓመት መጨረሻ ለአገልግሎት ክፍት ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን የሲዳማ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለፁ፡፡
የክልሉ መንግሥት ለሕዝቡ የመሠረተ-ልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት እየሠራ መሆኑን ያነሱት አቶ ደስታ፤ በዚህም በበጀት ዓመቱ የተጀመሩ የውኃ፣ የመንገድና የድልድይ ግንባታዎች እየተፋጠኑ ነው ብለዋል፡፡
የመሠረተ-ልማቶቹ ን ግንባታ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ለማድረግ ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ለኢዜአ ተናግረዋል፡፡
የተጀመሩ የውኃ ፕሮጀክቶች የክልሉን የመጠጥ ውኃ ሽፋን ወደ 65 በመቶ ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት እንደሚያግዙም ነው ያመላከቱት፡፡