Fana: At a Speed of Life!

ከ25 ቢሊየን ብር በላይ የግብር ታክስ ጉዳት በማድረስ የተከሰሰው በረከት አለኸኝ ጥፋተኛ ተባለ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 15፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) ከ25 ቢሊየን ብር በላይ የግብር ታክስ ጉዳት አድርሷል ተብሎ ክስ የቀረበበት በረከት አለኸኝ በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የሙስና ወንጀል ችሎት የጥፋተኝነት ፍርድ ተላለፈበት።

የፍትህ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ሕግ በረከት አለልኝ በተባለ ተከሳሽ ላይ በነሐሴ 26 ቀን 2015 ዓ.ም በሀሰተኛ ሰነድ የባንክ ሒሳብ መክፈት፣ በህገወጥ መንገድ ንግድ ፍቃድ ማውጣትና ማደስ፣ የታክስ አዋጁን መተላለፍ፣ ሀሰተኛ ሰነዶችን መጠቀም፣ የገቢ ደረሰኞችን አትሞ ለተለያዩ ነጋዴዎች ማሰራጨት የሚል ተደራራቢ ሰባት ክስ በዝርዝር ማቅረቡ ይታወሳል።

በተለይም በመስከረም 24 ቀን 2011 ዓ.ም እና በመስከረም 22 ቀን 2012 ዓ.ም ፍቃድ በማሳደስ የተመዘገበዉ በአስመጪነት ንግድ ስራ ዘርፍ ሆኖ ሳለ ምንም አይነት እቃ ከዉጭ ሳያስገባ እና የሀገር ዉስጥ የዕቃ ግዥ ሳይፈጽም ከወሰደው የሽያጭ መመዝገቢያ መሳሪያ ደረሰኞችን በማተም ለ339 ግብር ከፋዮች 1 ሺህ 663 ደረሰኞችን በማሰራጨት በ15 የገቢዎች ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ላይ 25 ቢሊየን 989 ሚሊየን 943 ሺህ 223 ብር ከ83 ሳንቲም ጉዳት ደርሷል በማለት ዐቃቤ ሕግ ካቀረባቸው ክሶች መካከል ጠቅሶ ነበር።

ዐቃቤ ሕግ በክስ ዝርዝሩ ላይ ከ30 ቢሊየን ብር በላይ ጉዳት ደርሷል በማለት ያቀረበው ዝርዝር ክስ ለተከሳሽ ከደረሰው በኋላ ግለሰቡ የወንጀል ድርጊቱን አለመፈጸሙን ጠቅሶ የዕምነት ክህደት ቃሉን በመስጠቱ፤ ዐቃቤ ሕግ 13 የሰው ምስክሮች እና 23 የሰነድ ማስረጃዎችን አቅርቧል።

ፍርድ ቤቱም የተሰሙ የሰው ምስክሮችን ቃልና የሰነድ ማስረጃዎችን መርምሮ ብይን ሰጥቶ ነበር።

በዚህም ፍርድ ቤቱ በ1ኛና በ2ኛ ክሶች ላይ ማለትም ሰለሞን ሙሉ ከውል በሚል የፈጠራ ስም በወጣ ሀሰተኛ የኗሪነት መታወቂያና ሀሰተኛ ውክልና መሰረት የንግድ ፍቃድ በማውጣትና በማሳደስ የተፈጸመ የወንጀል ድርጊት ተብሎ የቀረበውን ክስ በሚመለከት፣ ንግድ ፍቃድ መውጣቱንና መታደሱን እንጂ ሰለሞን ሙሉ ከውን በተባለው ሰው ወይም በተወካይ ንግድ ቢሮ ቀርቦ ንግድ ፍቃዱን ማን አወጣ ማን አሳደሰ ለሚለው አሳማኝ ማረጋገጫ ያልቀረበ መሆኑን አብራርቷል።

በተጨማሪም ከምስክሮች ቃል አሰጣጥ አንጻር በሰነዶች ማረጋጋጫ ተቋም አንድ ሰው በአካል ሳይቀርብ የጣት አሻራ ሳይሰጥና ሳይፈርም ውክልና እንደማይሰጥ መረዳቱን በመጥቀስ ሰለሞን ሙሉ ከውን በሚባል ሰው አሻራ ሰጥቶ ፈርሞ፣ በአካል ቀርቦ ውክልና የሰጠና ንግድ ፍቃድም ያወጣና ያሳደሰ መሆኑን ግምት መያዙን በማብራራት ከ1ኛ እና ከ2ኛ ክስ ነጻ ብሎታል።

ፍርድ ቤቱ 3ኛ እና 4ኛ ክስን በሚመለከት በ2010 እና በ2011 ዓ.ም ከውጭ ሀገር እቃ ሳያስገባና ምንም አይነት ሽያጭ ሳያከናውን ሀሰተኛ የተጭበረበሩ ሰነዶችን የአመታዊ የግብር ሪፖርትን ለግብር ሰብሳቢ መስሪያ ቤት ማስገባቱ መረጋገጡን በመጥቀስ 3ኛ ክስ ከ4ኛ ክስ ጋር ተጠቃሎ ተከሳሹ እንዲከላከል ብይን ተሰጥቷል።

በተጨማሪም ፍርድ ቤቱ ለ339 ግብር ከፋዮች 1 ሺህ 663 የገቢ ደረሰኞችን አትሞ በማሰራጨት የንግድ ትርፍ ፣ እና የተጨማሪ እሴት ታክስን ጨምሮ በ15 የገቢዎች ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ላይ 25 ቢሊየን 989 ሚሊየን 943 ሺህ 223 ብር ከ83 ሳንቲም ጉዳት መድረሱን በማስረጃ መረጋገጡን ገልጾ 5ኛ ክስንም ተከሳሹ እንዲከላከል ብይን ተሰጥቷል።

6ኛ ክስን ደግሞ ፍርድ ቤቱ ተከሳሹ በተከራየው ሱቅ ውስጥ ህገወጥ እውቅና የሌለው የሽያጭ መመዝገቢያ መሳሪያና ኮምፒውተሮች በገቢዎች ሰራተኞች ተገኝቷል ተብሎ የቀረበውን ክስ በሚመለከት የሽያጭ መመዝገቢያ መሳሪያው ከጁፒተር ንግድ ስራዎች ድርጅት የተገዛና የተገጠመ መሆኑን መረጋገጡን ችሎቱ ጠቅሶ እውቅና የሌለው ህገወጥ መሳሪያ ተገኝቷል በሚል በቀረበው ክስ ላይ ማስረጃ አለመቅረቡን ገልጾ ተከሳሹን ነጻ ነው ብሎታል።

7ኛ ክስን በሚመለከት የታክስ አስተዳደር አዋጅን በመተላለፍ ግብይት ሳይኖር ህገወጥ ደረሰኝ መጠቀም የሚለው ክስ ከ5ኛ ክስ ዝርዝር ጋር የሀሳብ መደራረብ ያለው መሆኑን ጠቅሶ ፍርድ ቤቱ በዚሁ 7ኛ ክስን በሚመለከት ነጻ በማለት ፍርድ ቤቱ ብይን ሰጥቷል።

ከዚህም በኋላ ፍርድ ቤቱ ተከሳሹ ያቀረበውን የመከላከያ ማስረጃ መርምሮና ከዐቃቤ ሕግ ማስረጃ ጋር አመዛዝኖ ዛሬ በዋለው ቀጠሮ የጥፋተኝነት ፍርድ ሰጥቷል።

በዚህም ፍርድ ቤቱ የተጠቀሰውን የወንጀል ድርጊት መፈጸሙን ማረጋገጡን ተጠቅሶ ጥፋተኛ ተብሏል።

የግራና ቀኝ ቅጣት አስተያየት መርምሮ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ፍርድ ቤቱ ለጥቅምት 27 ቀን 2017 ዓ.ም ተለዋጥ ቀጠሮ ሰጥቷል።

በታሪክ አዱኛ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.