Fana: At a Speed of Life!

አንዲት እናት በአንድ ጊዜ 4 ሕፃናት ተገላገሉ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 9፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) በፓዊ አጠቃላይ ሆስፒታል የ42 ዓመት ዕድሜ ያላቸው እናት በአንድ ጊዜ አራት ሕፃናትን ተገላገሉ።

ወይዘሮ አደባባይ የሺነህ ነዋሪነታቸው በአዊ ብሔረሰብ ዞን ጃዊ ወረዳ አሊኩራንድ ቀበሌ ሲሆን÷ በዛሬው እለት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ውስጥ በሚገኘው ፓዊ አጠቃላይ ሆስፒታል ነው ሶስት ወንድና አንድ ሴት የተገላገሉት።

ጨቅላ ህጻናቱ ጊዜያቸው ሳይደርስ በሰባት ወር የተወለዱ በመሆኑ በህፃናት ፅኑ ህሙማን ክፍል ክትትል እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡

በሆስፒታሉ መንታ መውለድና አልፎ አልፎም አንዲት እናት እስከ ሶስት ሕፃናትን በአንድ ጊዜ መገላገል የተለመደ ቢሆንም በአንድ ጊዜ አራት ሕፃናትን ሲወለዱ ግን የአሁኑ የመጀመሪያ መሆኑን ሚድዋይፈሪ ሞገስ ጌታቸው ተናግረዋል።

ወላጅ እናት የአሁኑን ጨምሮ ለስድስተኛ ጊዜ የወለዱ ሲሆን÷ በአሁኑ ሰዓት በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የህክምና ባለሙያው ገልጸዋል፡፡

ወ/ሮ አደባባይ በሰላም እንዲገላገሉ ለረዷቸው የሕክምና ባለሙያዎችና የፓዊ ወረዳ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ጽ/ቤት ምስጋና ማቅረባቸውን የፓዊ ወረዳ ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.