Fana: At a Speed of Life!

ለብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች የተለያዩ ሀገራዊና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሥልጠና እየተሰጠ ነው

አዲስ አበባ፣ መስከረም 4፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) ለብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች የተለያዩ ሀገራዊና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮረና የአመራር አቅምን በሚገነቡ ወቅታዊ ጉዳየች ዙሪያ ስልጠና መሰጠት ጀምሯል፡፡

ስልጠናውን የብልፅግና ፓርቲ ፕሬዚዳንት እና የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር ) አስጀምረዋል።

ስልጠናው “የሕልም ጉልበት ለእመርታዊ እድገት” በሚል መሪ ሃሳብ ነው እየተሰጠ የሚገኘው፡፡

በመድረኩ በሀገሪቱ የተመዘገቡ ውጤቶችን በላቀ ስኬት በመፈፀምና ተሞክሮን በማስፋት፣ ተግዳሮቶችን ወደ እድል በመቀየር የህዝብና የሀገርን ጥቅም ለማረጋገጥ በአመራሩ አቅም የሚያዝባቸው ጽሁፎች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው ይጠበቃል።

የብልፅግና ፓርቲ ከህዝቡ ጋር በመሆን በፈጸማቸው ተግባራት የተጎናፀፋቸውን አንፀባራቂ ድሎች ይበልጥ በማጎልበት በቀጣይ የሚያከናውናቸው የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ የጋራ አቋምና ዝግጁነት እንደሚፈጠርበትም ተመላክቷል፡፡

በጠንካራ ፓርቲ ጠንካራ የመንግስት አፈፃፀምን እውን በማድረግ ፓርቲው ለህዝብ የገባውን ቃል በተጨባጭ ለማሣካት ከፍተኛ አቅም የሚፈጥር ይሆናል መባሉንም የፓርቲው መረጃ ያመላክታል፡፡

እስከ መስከረም 15 ቀን 2017 ዓ.ም በሚቆየው ስልጠና ከሀገሪቱ ሁሉም ክልሎችና ሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች እንዲሁም ከፌዴራል ተቋማት የተውጣጡ ከ2 ሺህ በላይ የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.