Fana: At a Speed of Life!

የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ሀገርን ማረጋጋትና ማፅናት ያስቻሉ የመረጃ ስምሪቶችና የኦፕሬሽን ሥራዎች ማካሄዱ ተገለጸ

 

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 13፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ)የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ሀገርን ማረጋጋትና ማፅናት ያስቻሉ የመረጃ ስምሪቶችና የኦፕሬሽን ሥራዎች ማካሄዱ ተገለጸ።

አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ለመገናኛ ብዙኃን በላከው መግለጫ እንዳመለከተው፤ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጻም ሪፖርት እና የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ስትራቴጂክ አመራሮች በመሩት ግምገማዊ ውይይት ተካሄዷል።

በመድረኩም በማያቋርጥ ተቋማዊ ሪፎርም ሂደት ውስጥ የሚገኘው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የ2016 በጀት ዓመት አፈጻጸም ተቋሙ ካስቀመጣቸው ስትራቴጂካዊ ዕይታዎች አንጻር ስኬት የተመዘገበባቸው እንደነበር ተጠቁሟል።

ተቋሙ ከሌሎች የጸጥታና መረጃ ተቋማት ጋር በመቀናጀት ባከናወናቸው የተልዕኮ ሥራዎች ሀገራዊ የጸጥታ እና ደኅንነት ሁኔታ እንዲሻሻል በአጠቃላይ ሀገርን ማፅናት ያስቻለ አስተዋጽዖ ማበርከቱ በግምገማ መድረኩ ላይ ተገልጿል።

ተቋሙ መንግሥታዊ ስልጣንን በኃይል ለመያዝ በሚጥሩ ታጣቂ ኃይሎች ዙሪያ መረጃ በመሰብሰብና በመተንተን ለውሳኔ ሰጪ አካላት ግብዓት እንዲሆኑ ማድረጉም ተገልጿል።

መረጃዎቹን መሰረት በማድረግ የሕግ የበላይነትንና ተጠያቂነትን ማስፈን የሚያስችሉ የኦፕሬሽን ሥራዎች ተከናውነው ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ውለው በሕግ መጠየቃቸው ተመልክቷል።

በተለይም ደግሞ በአማራ እና በኦሮሚያ ክልሎች ያሉትን የጸጥታ ችግሮች ከመቅረፍ አኳያ የመረጃና የኦፕሬሽን ድጋፍ በመስጠት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማበርከቱ ተጠቁሟል፡፡

አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ የሚያመነጫቸውን መረጃዎች በአግባቡ በማይጠቀሙ አካላት ላይም ተገቢው የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ መደረጉንም መግለጫው አስታውቋል።

ከዚህ በተጨማሪም የተለያዩ የጦር መሣሪያዎች፣ ሐሰተኛ የውጭ ሀገራት ገንዘቦች፣ ኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች፣ ሐሰተኛ ብር ማተሚያ ማሽኖች፣ የከበሩ ማዕድናት፣ አደንዛዥ እጾችና ሌሎች የኮንትሮባንድ ዕቃዎች እንዲሁም በሕገወጥ ድርጊቱ የተጠረጠሩ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ መደረጉ በመግምገማው ወቅት ተመልክቷል።

ደኅንነትን ለማረጋገጥ በተሠሩ ሥራዎች የከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናትንና የቁልፍ መሰረተ ልማቶችን ደኅንነት ከማስጠበቅ በተጨማሪ፤ በዓመት ውስጥ የተከናወኑ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ሁነቶች እንዲሁም ትላልቅ ሀገራዊና አህጉራዊ ዝግጅቶች ያላንዳች የጸጥታ እንከን እንዲጠናቀቁ ያስቻሉ ሥራዎች መከናወናቸው ተገምግሟል።

ከዚህም በተጨማሪ ትኩረት ተሰጠቶት በተከናወነው የሪፎርም ስራ በአሰራር ስርዓት እንዲዘምን፤ በሰለጠነ የሰው ኃይል እንዲጠናከር እና ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ እንዲታጠቅ የተደረገው የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ዘርፍ በበጀት ዓመቱ ከ47 ሺ በላይ በረራዎች ሲከናወኑ እንዲሁም 9 ነጥብ 2 ሚልዮን መንገደኞች ሲጓጓዙ ያላንዳች የደኅንነት ስጋትና እንከን እንዲፈጸም አስተዋጽዖ ማበርከቱ በስኬትነት በመድረኩ መገምገሙ ተገልጿል።

የዓለምአቀፉ ሲሺል አቪዬሽን ድርጅት ከ12 ዓመት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የኢትዮጵያን የበረራ ደኅንነት በተመለከተ ኦዲት ማድረጉን ያስታወቀው መግለጫው፤ ድርጅቱ የሀገሪቱ የአቪዬሽን ደኅንነት ከየትኛውም አይነት ስጋት ነጻ መሆኑን ማረጋገጫ መስጠቱን በመገለጫው ተጠቁሟል።

ተቋማዊ ተልዕኮን ለማሳካት በሚያስችል መልኩ በተዘረጉ የትብብርና አጋርነት ሥራዎች በኮማንድ ፖስት ውስጥ የመሪነት ሚናን በመያዝ፤ ከጸጥታ ተቋማት ጋር በቅንጅት በመሥራትና መረጃዎችን በመለዋወጥ እንደ ሀገር ወቅታዊ ስጋቶችን መቀነስ መቻሉ ተብራርቷል።

በበጀት ዓመቱ የውስጥና የውጭ ተጽዕኖዎችን በመቋቋም የሚሰነዘሩ የሥነ-ልቦና ጦርነቶችን ከመመከት ባለፈ ወደ ማጥቃት የተሸጋገረ ተቋማዊ አቅም መፍጠር መቻሉም በመድረኩ ተገምግሟል።

አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ባከናወናቸው ሥራዎች እንደ ተቋም መረጃን የመሰብሰብ፤ የመተንተን እና የመመዘን አቅምን ማሳደግ የተቻለበት፤ ብሔራዊ ጥቅምን ሊያስጠብቁ የሚችሉ ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ስምሪቶች የተከናወኑበት፤ ቴክኖሎጂን መታጠቅ ብቻ ሳይሆን ማላመድና ማበልፀግ ላይ ትኩረት የተደረገበት፤ ሀብትን አቀናጅቶ መጠቀም ልምድ የዳበረበት መሆኑ እንደ ጥንካሬ ተነስቷል።

በ2016 በጀት ዓመት የተመዘገቡ ውጤቶችን ማስቀጠልን እና የተፈጠሩ ምልካም እድሎችን ማጠናከር በሚያስችል መልኩ የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ የተዘጋጀ መሆኑም ተጠቁሟል። ሆኖም ግን ከውስጥና ከውጭ ያሉ የሁኔታ አዝማሚያዎችን መሰረት በማድረግ መፈጸም እንደሚገባ አቅጣጫ ተቀምጧል።

በውስጥ የጸጥታ ሁኔታ መሻሻሎች መኖራቸው መልካም አጋጣሚዎችን ቢፈጥርም በቀጣናው የሚታየው አለመረጋጋት የመቀጠል አዝማሚያ እንደሚኖር መገመቱ፤ ዓለም አቀፋዊ ፖለቲካዊ ምህዳሩ ላይ የበላይነትን ለመቆጣጠር ሽኩቻ መጠናከሩ እንዲሁም ነባር የደኅንነት ስጋት የሆኑ ሽብርተኝነት፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች እና የጦር መሣሪያ ዝውውር አሁንም ስጋትነታቸው እንደሚቀጥል ከግምት መግባት እዳለበት ተገልጿል።

ተቋሙ በቀጣይ ዓመት ከውስጥና ከውጭ የሚሰነዘሩ የደኅንነት ስጋቶችን በመቀልበስ ሀገርን ማስቀጠል የሚያስችሉ የተልዕኮ ስራዎችን በስኬት ለመስራት በሚያስችል የሰው ኃይል፣ የቴክኖሎጂና የሎጀስቲክስ ቁመና ላይ እንደሚገኝ በግምገማዊ ውይይቱ ተጠቁሟል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.