Fana: At a Speed of Life!

ችግሮችን ለመፍታት መደማመጥና መነጋገርን ማስቀደም ይኖርብናል – አቶ አወል አርባ

አዲስ አበባ፣ የካቲት 2፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ችግሮችን ለመፍታት መደማመጥና መነጋገርን ማስቀደም ይኖርብናል ሲሉ የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ተናገሩ፡፡

“ሕብረ ብሔራዊ ወንድማማችነትና እህትማማችነት ለዘላቂ ሠላምና ሁለንተናዊ ብልፅግና” በሚል መሪ ሃሳብ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በጅማ ከተማ ውይይት ተካሂዷል።

በመድረኩ የተገኙት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ÷ችግሮችን ለመፍታት መደማመጥና መነጋገርን ማስቀደም ይኖርብናል ብለዋል።

ዘላቂ ሠላምን በማረጋገጡ ረገድም ቅንጅታዊ ስራን ማጎልበት ይገባል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ÷ በግጭትና ጦርነት የሚጠቀሙ አሉና እንቅስቃሴያቸውን በጋራ ልንታገለው ይገባል ሲሉ ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ብዝሃነት ጎልቶ የሚታይባት ሀገር ከመሆኗም በላይ የበርካታ ሃብቶች ባለቤት መሆኗን ያወሱት አቶ አወል÷ ፈጣሪ የሰጠንን ፀጋ በመለየት ተግተን ልንሰራ ይገባል ነው ያሉት፡፡

የብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር) በበኩላቸው÷ብልፅግና ፓርቲ የሕዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ሥራዎች እየከወነ ነው፤በዲፕሎማሲ፣በምጣኔ ሃብት እና በማህበራዊ ጉዳዮች ላይ አመርቂ ውጤት አስመዝግቧል ብለዋል።

መንግስት የዜጎችን ሠላምና ደህንነት ለማስጠበቅ ቁርጠኛ መሆኑንም አረጋግጠዋል።

የጨፌ ኦሮሚያ አፈጉበዔ ወ/ሮ ሰዓዳ አብዱረህማን÷ የዞኑን ሠላምና ፀጥታ ለማረጋገጥ ነዎሪዎቹ ከአመራሮች ጋር በመቀናጀት የሰራችሁት ስራ የሚደነቅ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

በተለያዩ ዘርፎች የተነሱት ሃሳቦች ለቀጣይ ሥራ ስንቅ መሆኑን የተናገሩት አፈጉባዔዋ÷ በክልሉ ሰላምን ለማረጋገጥ የሚሰራው ስራ ሕብረተሰቡን በማሳተፍ በቁርጠኝነት እንደሚቀጥልም ጠቁመዋል፡፡

በወንድሙ አዱኛ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.