Fana: At a Speed of Life!

በአማራ ክልል የተከናወነው ሕግ የማስከበር ሥራ የጠላትን ቅስም የሰበረ ነው – የክልሉ መንግስት ኮሙኒኬሽን

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 24፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በአማራ ክልል ላለፉት ሶስት ሳምንታት የተከናወነው ሕግ የማስከበር ሥራ የጠላትን ቅስም የሰበረ መሆኑን የክልሉ መንግስት ኮሙኒኬሽን አስታወቀ፡፡

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ግዛቸው ሙሉነህ ዛሬ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በመግለጫቸውም÷ ሕገወጥነትና ስርዓት አልበኝነትን በማጀገን ክልሉን የትርምስ ማዕከል ለማድረግ  የተወጠነውን ሴራ ማክሸፍ የቻለ የሕግ ማስከበር ስራ መሠራቱን አንስተዋል፡፡

መንግስት ሕግና ስርዓት የማስከበር አቅም እንዳጣ በማስመሰል፣ ሕዝባዊ ቁጣ እንዲነሳና ከፍተኛ ሁከት እንዲፈጠር ለማድረግ የተሴረው ሴራ ከሽፏል ነው ያሉት የኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊው።

የፀጥታ ኃይሉ ራሱን መስዋዕት በማድረግ ሕግ የማስከበር ተገቢ ሚናውን እየተወጣ መሆኑን ገልጸው፣ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች ሕዝቡ ከስጋት እፎይ እንዲል ማድረግ መቻሉንም ጠቁመዋል።

ጠላት÷ ብሔርን ከብሔር፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት የማጋጨት ስልትን በመጠቀም በአማራ ክልል ሁከት ለመፍጠር እና ለዳግም ወረራ ክልሉን ለማዳከም ጥረት ቢያደርግም÷ የውስጥ አንድነትን ማረጋገጥ የቻለ የሕግ ማስከበር ሥራ ተሰርቷል ብለዋል።

በጋራ ዘመቻ ሂደቱም በቀጥታ 6 ሚሊየን የሚሆኑ ዜጎችን ማሳተፍ መቻሉንም ነው አቶ ግዛቸው የገለጹት፡፡

በሕግ ማስከበር ሥራው በክልሉ ሕገ ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውር እንዳይኖር መደረጉን እና በሽፍቶች የሚፈፀም ዘረፋና ስርቆትን መቀነስ መቻሉንም ተናግረዋል ።

በበርናባስ ተስፋዬ

ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

 

 

 

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.