Fana: At a Speed of Life!

አሸባሪውን የሸኔ ቡድን በዓለም አቀፍ ደረጃ በማስተዋወቅ የተጠረጠሩ ጋዜጠኞች በቁጥጥር ስር ዋሉ

አዲስ አበባ ፣ ታህሳስ 6 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የፌደራል ፖሊስ አሸባሪውን ሸኔ በዓለም አቀፍ ደረጃ በማስተዋወቅ የተጠረጠሩ የአሶሽየትድ ፕረስ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታወቀ።

በኮሚሽኑ በወንጀል ምርመራ ቢሮ የሽብር ወንጀሎች ምርመራ ዲቪዥን ሃላፊ ኢንስፔክተር ተስፋዬ ኦላኒ፥ ተጠርጣሪዎቹ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሸባሪ የተባለ ቡድን እውቅና እንዲያገኝ በማድረግ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተናግረዋል።

በቁጥጥር ስር የዋሉት ተጠርጣሪዎች አንደኛ አሚር አማን፣ ሁለተኛ ተጠርጣሪ ቶማስ እንግዳ እና ሦስተኛ ተጠርጣሪ አዲሱ ሙሉነህ ናቸው።

ጋዜጠኞቹ ኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ ዞን ሚዳ ቀኝ ወረዳ የሚንቀሳቀሰውን የሽብርተኛውን ሸኔ ቡድን ወታደራዊ እንቅስቃሴ ተከታትሎ በመቅረጽና ቃለ መጠይቅ በማድረግ መረጃዎችን በማሰባሰብ ኬንያ ለሚገኘው እና የአሶሽየትድ ፕረስ የምስራቅ አፍሪካ ተወካይ ለሆነው ግብጻዊው ካሊድ ካዚሃ በመላክ በቁጥጥር ስር መዋላቸውንም ነው የተናገሩት።

ተጠርጣሪዎቹ ከአዲስ አበባ በመንቀሳቀስና የሽብር ቡድኑን እንቅስቃሴ ቀርጸው እንዲመጡ ከግብጻዊው ጋዜጠኛ ጋር ግንኙነት በመፍጠር ጉዳዩ ዓለም አቀፍ በሆነው አሶሽየትድ ፕረስ እንዲተላለፍ ማድረጋቸውንም ጠቁመዋል።

ወቅቱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የታወጀበትና የተለያዩ ምዕራባውያን መገናኛ ብዙሃን በወቅቱ አዲስ አበባ ተከባለች፤ ህወሓትና ሸኔ ወደ አዲስ አበባ እየገሰገሱ ነው፤ በሚል ወሬ የሚያናፍሱበትና ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በአገር ላይ የተቃጣውን አደጋ ለመቀልበስ ወደ ግንባር በዘመቱበት ወቅት ተጠርጣሪዎቹ ሆን ብለውና አስበውበት ህዝቡን ለማሸበር ቀረጻው በዓለም አቀፍ ሚዲያ እንዲተላለፍ በማድረጋቸው በቁጥጥር ስር መዋላቸውንም አስረድተዋል።

ተጠርጣሪዎቹ አሸባሪው ቡድን እንዲታወቅ የሚዲያ ተልዕኮ ተቀብለው ህዳር 16 ቀን ወደ ስፍራው በማቅናት እስከ ህዳር 18 ቀን 2014 ዓ.ም ቀረጻ በማከናወን እና ፕሮዳክሽን በመስራት ከላኩ በኋላ በመኖሪያ ቤታቸው እና በስራ ገበታቸው ህዳር 19 ቀን 2014 ዓ.ም በቁጥጥር ስር ውለዋል።

በወቅቱም በእጃቸው ከተገኙት ላፕቶፕ እና ተንቀሳቃሽ ስልኮች በርካታ ማስረጃዎች መገኘታቸውንም አስረድተዋል።

ጋዜጠኞቹ ረጅም ርቀት ተጉዘው ያደረጉት ቀረጻ በወቅቱ በኢትዮጵያ ላይ ይነዛ የነበረውን ፕሮፓጋንዳ ለመደገፍ ሆን ተብሎ የተዘጋጀ መሆኑንም ገልጸዋል።

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.