የሀገር ውስጥ ዜና

የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ተቋማት ለተፈናቃዮች አስቸኳይ እርዳታ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀረበ

By Tibebu Kebede

September 19, 2021

 

አዲስ አበባ መስከረም 9፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ተቋማት ለተፈናቃዮች አስቸኳይ እርዳታና ድጋፍ እንዲያደርጉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባዔ ሽታዬ ምናለ ጥሪ አቀረቡ።

በአሸባሪው ህወሃት ወረራ ተፈናቅለው ደሴ ከተማ ለተጠለሉ ዜጎች ምክትል አፈ-ጉባኤ ሽታዬ ምናለን ጨመሮ ሴት ሚኒስትሮች፣ ከፍተኛ አመራሮችና ባለሃብቶች ድጋፍ አድርገዋል።

ሴቶችና ህፃናት አጠቃላይ ንጹኃን ዜጎች በእንዲህ አይነት ሁኔታ ተጎሳቁለውና ለከፋ ችግር ተጋልጠው ማየት አሳዛኝ መሆኑን የገለጹት ምክትል አፈ-ጉባኤዋ፤ “ለተቸገረ ቀድሞ ደራሹና አብሮ መብላት፣ እንግዳ መቀበል የሚያውቅበት ደጉ የወሎ ህዝብ በአሸባሪው ግፍ ተፈናቅሎ ለከፍተኛ ችግር ተዳርጎ ይገኛል” ብለዋል።

በተለይም እናቶችና ህፃናት ተፈናቅለው በከፋ ችግር ውስጥ ላይ የሚገኙ በመሆኑ የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ተቋማት በደሴ ከተማ ተጠልለው ለሚገኙ ዜጎች አስቸኳይ እርዳታና ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።

“ተፈናቃዮቹ የምግብ፣ የጤና፣ የመጠለያ እና ሌሎች መሰረታዊ ድጋፎች ያስፈልጓቸዋል” ብለዋል ምክትል አፈ ጉባኤዋ።

በጉብኝቱ ለእናቶችና ህፃናት ኃይል ሰጪ ምግብን ጨምሮ ማኮረኒና ዘይት እንዲ ሌሎችም ምግብ እና ምግብ ነክ ያልሆኑ ቁሳቁሶች ድጋፍ እንደተደረገላው የኢዜአ ዘገባ ያመለክታል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!