ዓለምአቀፋዊ ዜና

በአሜሪካ በተከሰተ አውሎ ንፋስ የ45 ሰዎች ሕይወት አለፈ

By Alemayehu Geremew

September 03, 2021

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 28፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ)አራት የአሜሪካ ሰሜን ምስራቅ ግዛቶች በአውሎ ንፋስ መመታታቸው ተገለጸ፡፡

በተከሰተው አደጋም እስከ አሁን የ45 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ነው የተመላከተው፡፡

የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን ጉዳዩን አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት÷ አሜሪካ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር በተያያዘ የተለያዩ ችግሮችን እየተጋፈጠች መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ፕሬዚዳንቱ የአየር ንብረት ቀውስ ያስከተለውን የጎርፍ መጥለቅለቅ እና አውሎ ንፋስ አደጋ ለመቋቋም ከፍተኛ መዋዕለ ነዋይ መድቦ መስራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል፡፡

የተጋረጠውን አደጋ የተለያዩ ስልቶችን በመንደፍ መታገል እና ሁኔታውን መቀልበስ ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡

ኒውዮርክ እና ኒው ጀርሲ በታሪካቸው ታይቶ የማይታወቅ የዝናብ መጠን ያጋጠማቸው ሲሆን÷ በአካባቢው የሚገኙ አንዳንድ ቤቶች እና መኪናዎችም ዝናቡ ባስከተለው ጎርፍ መዋጣቸው ተመላክቷል፡፡

አደጋውን ተከትሎም በኒውዮርክና ኒውጀርሲ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የታወጀ ሲሆን÷ይህም ከፌዴራሉ መንግስትለአደጋው መቋቋሚያ የገንዘብ ድጋፍ እንዲያገኙ ያስችላል ተብሏል፡፡ ምንጭ ÷ ቢቢሲ