Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

በእምነት ተቋማት፣ በገበያና በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የኮቪድ-19 መከላከያ መንገድ በአግባቡ እንዲተገበር ተጠየቀ

አዲስ አበባ ፣ ሚያዝያ 22 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ)በእምነት ተቋማት፣ በገበያና በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የኮቪድ-19 መከላከያ መንገድ በአግባቡ እንዲተገበር የጤና ሚኒስትር ዶክተር ሊያ ታደሰ አሳስበዋል።
ሚኒስትሯ የስቅለትና ፋሲካ በዓላትን በማስመልከት ባስተላለፉት የኮቪድ-19 የጥንቃቄ መልእክት “ወቅቱ የላብራቶሪ ምርመራ ከሚደረግላቸው መካከል በየቀኑ ከ1 ሺህ ሰዎች በላይ በቫይረሱ የሚያዙበትና በከፋ የሚታመሙበት ነው” ብለዋል።
ችግሩ ከጤና አልፎ ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶች እያሰከተለ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
“በመሆኑም አሁንም ሕብረተሰቡ የመከላከያ መንገዶቹን ሳይታክትና የሚቆጣጠረውን አካል ሳይጠብቅ መተግበር ይኖርበታል” ብለዋል።
በተለይም በእምነት ተቋማት፣ በገበያና በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የኮቪድ-19 መከላከያ መንገድ በአግባቡ እንዲተገበር አሳስበው ሰሞኑን በሚከበሩ ሐይማኖታዊ በዓላት ላይም አስፈላጊው የመከላከያ ጥንቃቄ እንዲደረግ ጠይቀዋል።
በሌላ በኩል እስከ ትናንት ድረስ ከ1 ሚሊዮን በላይ ሰዎች የመጀመሪያ ዙር የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባትን መውሰዳቸውን ያነሱት ሚኒስትሯ የክትባት መስፈርቱን የሚያሟሉ ዜጎች ሁሉ ክትባቱን ሊወስዱ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ ወረርሺኙን ፊት ለፊት እየተዋጉ ለሚገኙ የጤና ሙያተኞች ምስጋና ማቅረባቸውን ከጤና ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡-https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
Exit mobile version