የሀገር ውስጥ ዜና

የኢትዮጵያ የዲጂታል መሰረተ ልማት ግንባታ ለአፍሪካ ሀገራት ትምህርት እንደሚሆን ተጠቆመ

By Adimasu Aragawu

March 26, 2025

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 17፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ሀገራት ትምህርት የሚሆን የዲጂታል ኢኮኖሚና መሰረተ ልማት እየገነባች መሆኑን በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ገለጸ፡፡

በኮሚሽኑ የፈጠራና ቴክኖሎጂ ክፍል ኃላፊ ማክታር ሳክ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ በሰጠችው ትኩረት በስራ ዕድል ፈጠራና በኢንቨስትመንት ፍሰት እመርታዊ ለውጥ እያስመዘገበች እንደምትገኝ ተናግረዋል።

የበይነ መረብ ግንኙነት ዕድገት ለአህጉሪቱ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት መሳካት ወሳኝ በመሆኑ ለአፍሪካውያን ተመጣጣኝ አገልግሎት ማቅረብ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።

ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ በዲጂታል መሰረተ ልማትና ኢኮኖሚ ግንባታ ለአፍሪካውያን ትምህርት የሚሆን ስኬት እያስመዘገበች ነው ብለዋል።

በቀጣይም ከዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ምርትና አገልግሎት ሰጪዎች ጋር በመተባበር የዕውቀትና ክህሎት ሽግግር ላይ በትኩረት መስራት እንደሚገባ ማንሳታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ኢትዮጵያ የመንግስትን የመፈፀም አቅም በማሳደግ ጠንካራ የኢኮኖሚ ዕድገት በመፍጠር አስደናቂ የልማት እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኗንም ማክታር ሳክ (ዶ/ር) ገልጸዋል።