በአዲስ አበባ የንግድ ተቋማት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ከ30 አገልግሎት መስጠት ጀመሩ
አዲስ አበባ፣ ታሕሣሥ 9፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በአዲስ አበባ የንግድ ተቋማት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ከ30 አገልግሎት የሚሰጡ መሆኑን የከተማዋ ንግድ ቢሮ አስታወቀ።
የቢሮው ኃላፊ ሀቢባ ሲራጅ የንግድ ተቋማት የሥራ ሰዓት መራዘምን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ÷ በከተማዋ ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በተለይም የኮሪደር ልማት ባለባቸው አካባቢዎች የንግድ ተቋማት እስከ ምሽቱ 3 ሰዓት ከ30 አገልግሎት እንዲሰጡ የአስተዳደሩ ካቢኔ መወሰኑን ገልጸዋል።
ከተወሰነበት እለት ጀምሮ አሰራሩ ተግባራዊ መደረጉን ጠቅሰው÷ ይህም የከተማዋን ኢኮኖሚ የሚያነቃቃና የንግዱን ማኅበረሰብ ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው ብለዋል።
ከንግድ ተቋማት ባለፈ የመንግሥት እና የግል ትራንስፖርት አገልግሎት እስከ ምሽቱ 4 ሰዓት አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉንም ገልጸዋል።
በከተማዋ ባለፋት አምስት ወራት ከ47 ሺህ በላይ ነጋዴዎች አዲስ ንግድ ፍቃድ ማውጣታቸውን የጠቀሱት ኃላፊዋ÷ የንግድ ፈቃዳቸውን ያላደሱ ነጋዴዎችም በአፋጣኝ እንዲያድሱ ማሳሰባቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡