የሀገር ውስጥ ዜና

የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትን መደገፍ ሀገርን መደገፍ ነው – የመከላከያ ሠራዊት የክብር አባላት

By ዮሐንስ ደርበው

October 25, 2024

 

 

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 15፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊትን መደገፍ ሀገርን መደገፍ ነው ሲሉ የመከላከያ ሠራዊት የክብር አባላት ገለፁ።

 

በ117ኛው የሠራዊት ቀን በዓል ላይ ለሚዲያ ባለሙያዎች፣ ለጋዜጠኞችና ለማህበረሰብ አንቂዎች የመከላከያ ሠራዊቱ የክብር አባልነት ተሰጥቷቸዋል።

 

በዚሁ መሰረት  በላይ መንገሻ፣ ዑሥታዝ ጀማል በሽር፣ መሐመድ ቢን መሐመድ አል አሩሲ እንዲሁም ጋዜጠኛ እና ደራሲ ውብሸት ታዬ የክብር አባልነት ዕውቅና የተሰጣቸው ናቸው፡፡

 

ሙያቸውን እና እውቅናቸውን ተጠቅመው ሀገርን እና ሠራዊቱን ከውጭና ከውስጥ ፀረ ሰላም ሀይሎች የስም ማጥፋት ዘመቻ በመታደጋቸው ላደረጉት ድንቅ ተግባር የክብር አባልነት እንደተሰጣቸው በመድረኩ ተገልጿል።

 

አባላቱም “ሠራዊታችንን መደገፍ ሀገርን መደገፍ በመሆኑ እና የሠራነው ስራ ደግሞ ሠራዊታችን ለኛ ከሚከፍለው ዋጋ አንፃር ለሽልማት የሚያበቃን ባይሆንም ይህ ታላቅ ተቋም ስራችንን ተመልክቶ ላበረከተልን ሽልማት ምስጋናችንን እናቀርባለን” ብለዋል።

 

በቀጣይም አባል ስለሆንን ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያዊነት ግዴታችን በመሆኑ የበለጠ እንሰራለን ማለታቸውንም ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት  ማህበራዊ ትሰስር ገፅ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡