አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 12፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ)የጉምሩክ ኮሚሽን ከጥቅምት 1 እስከ 7 ቀን 2017 ዓ.ም ባደረገው ክትትል ከ428 ሚሊየን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸው የኮንትሮባንድ እቃዎች መያዛቸው ተገለፀ፡፡
ከዚህም ውስጥ 134 ነጥብ 3 ሚሊየን ብር የገቢ የኮንትሮባንድ እቃዎች ሲሆኑ÷ 294 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር የሚገመቱት ደግሞ የወጭ የኮንትሮባንድ እቃዎች መሆናቸው ተገልጿል፡፡
ከተያዙት የኮንትሮባንድ እቃዎች መካከል አልባሳት፣ ኤሌክትሮኒክስ፣ የግንባታ እቃዎች፣ ቡና፣ ጥራጥሬ፣ የተሽከርካሪ መለዋወጫ፣ የመዋቢያ እቃዎች፣ ጫት፣ አደንዛዥ እጾች ፣ መድኃኒት፣ የምግብ ዘይት ፣ የተለያዩ ተሽከርካሪዎች እና የውጭ ሀገር ገንዘቦች ይገኙበታል፡፡
በተጠቀሰው ጊዜ የገቢ እና የወጭ ኮንትሮባንድን በመቆጣጠር ሀዋሳ፣ ሞያሌ እና ድሬድዋ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዙ የኮሚሽኑ መረጃ ያመላክታል፡፡