የሀገር ውስጥ ዜና

የአፍሪካ ሀገራት ሚኒስትሮችና ወታደራዊ አታሼዎቹ የመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪን ጎበኙ

By Shambel Mihret

October 16, 2024

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 6፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) የአፍሪካ ሀገራት ሚኒስትሮችና ወታደራዊ አታሼዎቹ በመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ስር የሚገኙ ልዩ ልዩ ፋብሪካዎችን ጎብኝተዋል፡፡

በጉብኝቱ ወቅት ስለ ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽኑ ፋብሪካዎች ዝርዝር ተግባርም ገለፃ ተደርጓል ተብሏል፡፡

ኢንዱስትሪው ልዩ ልዩ የውጊያ ብረት ለበስ ተሽከርካሪዎችን በመጠገን፣ አቅማቸውን በማሻሻልና በማምረት የሚሰራው ስራ ሀገር የሚያኮራ እንደሆነ የመከላከያ ሚኒስትሮቹ ጠቁመዋል።

በጉብኝቱ የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሐመድ፣ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም አማካሪና የተኩስ አመራር ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል አለምሸት ደግፌና ከፍተኛ መኮንኖች ተሳትፈዋል።

በዚሁ ወቅት ኢንጅነር አይሻ መሐመድ÷ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ሀገሮች መከላከያ ሚኒስትሮች ያላትን ልምድ በማካፈል ረገድ የቀዳሚነቱን ስፍራ መውሰድ መቻሏን አስገንዝበዋል።

የመከላከያ ሚኒስትሮቹ እና ወታደራዊ አታሼዎቹ በኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽኑ ቅጥር ግቢ ውስጥ ለየሀገሮቹ ተለይቶ በተዘጋጀላቸው ቦታ ላይ ችግኝ በመትክል አሻራቸውን እንዳኖሩም የሀገር መከላከያ ሠራዊት ማህበራዊ ትስስር ገጽ መረጃ ያመላክታል፡፡