Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

የፐርፐዝ ብላክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍስሐ እሽቱን (ዶ/ር) ጨምሮ 10 ግለሰቦች በማታለል ሙስና ወንጀል ተከሰሱ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 4፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) የፍትሕ ሚኒስቴር የሙስና ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ሕግ የፐርTዝ ብላክ ኢቲኤች ትሬዲንግ አ.ማ የቦርድ አባልና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍስሐ እሽቱን (ዶ/ር) ጨምሮ በ10 ግለሰቦች እና ሁለት ድርጅቶች ላይ ክስ መስርቷል።

ክሱ የተመሰረተው በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 3ኛ የሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ነው።

ተከሳሾቹ 1ኛ የፐርTዝ ብላክ ኢቲኤች ትሬዲንግ አ.ማ የቦርድ አባልና ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍስሐ እሽቱ (ዶ/ር)፣2ኛ የተቋሙ ም/ስራ አስፈጻሚ ኤርሚያስ ብርሃኑ (ዶ/ር)፣ 3ኛ የተቋሙ ቺፍ  ኦፕሬሽን ኦፊሰር እና የቦርድ አባል ወ/ሮ ኤፍራታን ነጋሽን ጨምሮ በአጠቃላይ 10 ግለሰቦች እንዲሁም ፐርፐዝ ብላክ ኢቲኤች ትሬዲንግ እና ኖትር ዲዛይን ሃ/የተ/የግ/ማህበር ናቸው፡፡

ተከሳሾቹ በአዲስ አበባ ከተማ መሃል ሜክሲኮ ላይ በ100 ካሬ ሜትር ይዞታ ላይ  ባለ 3 መኝታ ቤት መኖሪያ ቤት  በ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር የሚሸጥ መሆኑን በሚዲያ በማስተዋወቅ ሰዎች ቤት ለመግዛት ሲሄዱ “መጀመሪያ ገንዘቡን አስገቡና ውሉን ትመለከታላችሁ “በማለት ከሌሎች ግብረዓበሮቻቸው ጋር በመሆን አሳሳች ቃላቶችን በመጠቀም፣ ሰዎች ገንዘቡን ካስገቡ በኋላ ደግሞ የአክሲዮን ግዢ ውል እንዲፈርሙ በማድረግ ምንም አይነት የግንባታ ቦታ ባልተረከቡበት ሁኔታ 2 ቢሊየን 234 ሚሊየን 200 ሺህ ብር በመሰብሰብ፣ ቤቱን ሰርተው ሳያስረክቡ በመቅረት እንዲሁም ግማሹን ገንዘብ ወደ ውጭ እንዲሸሽ በማድረግ፣ ኮሚሽን በመቀበልና በማታለል  ወንጀል ተጠርጥረው  በአዲስ አበባ ፖሊስ በኩል በጊዜ ቀጠሮ መዝገብ የምርመራ ማጣሪያ ሥራ ሲከናወን እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል።

በዚህ መልኩ ፖሊስ  ሲያከናውነው የቆየው የምርመራ ማጣሪያ ሥራ መጠናቀቁን ተከትሎ በዛሬው ዕለት ዐቃቤ ሕግ ተደራራቢ ዝርዝር ክሶችን  በየደረጃቸው  አቅርቦባቸዋል።

ከቀረቡ ክሶች መካከል በአንደኛው ክስ ላይ ከ1ኛ-9ኛ ባሉ ተከሳሾች ላይ እንደተመላከተው፤ በኢፌዲሪ የወጣውን የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1) (ሀ) እና (ለ)  እንዲሁም  የሙስና ወንጀሎችን ለመደንገግ አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀጽ 32 (2) ላይ የተመላከተውን ድንጋጌ መተላለፍ የሚል ክስ ይገኝበታል።

እንደ አጠቃላይ በቀረበው ተደራራቢ ክስ ዝርዝር ችሎት ለቀረቡ 4 ተከሳሾች ዝርዝሩ እንዲደርሳቸው የተደረገ ሲሆን ÷የተከሳሾቹ ጠበቆች በደንበኞቻቸው ላይ የቀረበውን ክስ ዝርዝር ተመልክተው ዋስትና ላይ ክርክር ለማድረግ ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

ፍርድ ቤቱም ዋስትና ላይ የሚደረገውን የግራ ቀኝ ክርክር ለመከታተል ለፊታችን ሰኞ ጥቅምት 11 ቀን 2017 ዓ.ም ተዋጭ ቀጠሮ በመስጠት ችሎት ያልቀረቡ ተከሳሾችን ፖሊስ በአድራሻቸው አፈላልጎ እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

በታሪክ አዱኛ

Exit mobile version