ዓለምአቀፋዊ ዜና

የቱርክ አየር መንገድ ፓይለት አውሮፕላን እያበረረ ህይወቱ አለፈ

By ዮሐንስ ደርበው

October 09, 2024

አዲስ አበባ፣ መስከረም 29፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) የቱርክ አየር መንገድ አብራሪ ከአሜሪካ ሲያትል ተነስቶ ወደ ቱርክ ኢስታንቡል የሚጓዝ አውሮፕላን በማብረር ላይ እያለ ህይወቱ ማለፉ ተነገረ፡፡

የ59 ዓመቱ አውሮፕላን አብራሪ ኢልሴሂን ፔሊቫን በበረራ ላይ እያለ በህመም በመውደቁ ረዳት አብራሪው አውሮፕላኑን ያለምንም ችግር ማሳረፉን የቱርክ አየር መንገድ ቃል አቀባይ ያህያ ኡስቱን በኤክስ ገጻቸው አስታውቀዋል፡፡

ለአብራሪው የመጀመሪያ ደረጃ የህክምና እርዳታ በማድረግ ለተሻለ ህክምና እንዲደርስ የተደረገው ጥረት ሳይሳካ መቅረቱ ተገልጿል።

ረዳት አብራሪው አውሮፕላኑን በፍጥነት በማሳረፍ ለዋና አብራሪው እርዳታ ለማድረግ ቢሞከርም ህይወቱን ማትረፍ እንዳልተቻለ ቃል አቀባዩ ገልጸዋል።

ወደ ኢስታንቡል በመብረር ላይ የነበረው ኤርባስ350 አውሮፕላን ባጋጠመው የአብራሪው ድንገተኛ ህመም የተነሳ በኒውዮርክ ማረፉን ተናግረዋል።

በቱርክ አየር መንገድ ውስጥ ከ2007 ጀምሮ በአብራሪነት ሲሰራ የቆየው አብራሪው ባለፈው መጋቢት ወር ባደረገው የጤና ምርመራ ስራውን ለመስራት የሚከለክል የጤና እክል እንደሌለበት መረጋገጡንም ጠቅሰዋል።

ፔሊቫንን ለሞት ያበቃው የጤና ችግር እስካሁን ምን እንደሆነ አለመታወቁን ቢቢሲ ዘግቧል።

ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ አደጋ ያጋጠመው በፈረንጆቹ 2015 ሲሆን፤ ዕድሜው 57 የሆነ አብራሪ ከፎኒክስ ወደ ቦስተን በማብራር ላይ ሳለ ህይወቱ ማለፉ ይታወሳል።