የሀገር ውስጥ ዜና

አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 5 ሺህ 300 ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር መዘጋጀቱን አስታወቀ

By Meseret Awoke

October 02, 2024

አዲስ አበባ፣መስከረም 22፣ 2017(ኤፍ ቢ ሲ) አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዘንድሮ 5 ሺህ 300 የቅድመ መደበኛ ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር መዘጋጀቱን የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ጄሎ ኡመር (ዶ/ር) አስታወቁ፡፡

የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ነጥብ አስመዝግበው በመንግሥት ሙሉ ወጪ የሚማሩ 4 ሺህ 402 ተማሪዎች ለውድድር ተመዝግበው 2 ሺህ 660 ፈተናውን እንዳለፉም ገልጸዋል።

የዩኒቨርሲቲ የመግቢያ ነጥብ በማምጣትና በራሳቸው ከፍለው ለመማር ካመለከቱት 7 ሺህ 537 ተማሪዎች መካከል ደግሞ 2 ሺህ 640 ተማሪዎች የመግቢያ ፈተናውን አልፈዋል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ ዓመት ዩኒቨርሲቲው 5 ሺህ 300 ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር መዘጋጀቱን ገልጸው÷ ከእነዚህ መካከል ከ500 በላይ ውጤት ላስመዘገቡ 200 ተማሪዎች ነጻ የትምህርት ዕድል እንደሚሰጥ አረጋግጠዋል።

በአዲሱ የተማሪዎች ቅበላ መስፈርት መሰረት ሴቶችንና አካል ጉዳተኞችን በልዩ ሁኔታ ተጠቃሚ የሚያደርጉ አሠራሮች እየተተገበሩ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡