Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

የሃማስ መሪ እስራኤል በሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት ተገደለ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 20፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) በሊባኖስ የሃማስ መሪ ፋትህ ሻሪፍ አቡ አል አሚን እስራኤል በፈጸመችው የአየር ጥቃት መገደሉን ቡድኑ አስታውቋል፡፡

ሃማስ ጉዳዩን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ÷ፋትህ ሻሪፍ አቡ አል አሚን እስራኤል በደቡብ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት አብረውት ከነበሩ የቅርብ ቤተሰቦቹ ጋር መገደሉን አረጋግጧል፡፡

የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት በሊባኖስ ታጣቂ ቡድን ሂዝቦላህ ላይ የሚፈጽመውን የአየር ላይ ጥቃት አጠናክሮ መቀጠሉን ገልጿል፡፡

በትናንትናው ዕለት የእስራኤል ጦር በሊባኖስ በፈጸመችው የአየር ላይ ጥቃት ነቢል ኳዑክ የተባለ የሂዝቦላህ ቁልፍ ከፍተኛ አመራር መግደሉን አስታውቋል፡፡

በተጨማሪም ባሳለፍነው ዓርብ ዕለት በሊባኖስ በተፈጸመ ጥቃት የሂዝቦላህን መሪ ሀሰን ነስራላህን ጨምሮ 20 የሂዝቦላህ ከፍተኛ አመራሮች መገደላቸውን ሬውተርስ በዘገባው አስታውሷል፡፡

Exit mobile version