Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

ኢትዮጵያ ለኢጋድ ዘላቂ የቱሪዝም ፍኖተ ካርታ ትግበራ ግንባር ቀደም ሚናዋን እንደምትወጣ አረጋገጠች

አዲስ አበባ፣ መስከረም 8፣ 2017 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ ለምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ዘላቂ የቱሪዝም ፍኖተ ካርታ ትግበራ ግንባር ቀደም ሚናዋን እንደምትወጣ የቱሪዝም ሚኒስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ ተናገሩ።

የኢጋድ አባል ሀገራት የቱሪዝም ሚኒስትሮች በቀጠናው ለቀጣይ አስርት ዓመታት ተግባር ላይ ይውላል በተባለው እና ነገ ይፋ በሚደረገው “የኢጋድ ዘላቂ የቱሪዝም ፍኖተካርታ” ላይ እየተወያዩ ነው።

በውይይቱ መክፈቻ ላይ ንግግር ያደረጉት የቱሪዝም ሚኒስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ÷ በቀጠናው የዓለም አቀፍ ጎብኝዎችን ማሳደግ የሚያስችል አቅምን መፍጠር የሚያስችል ፍኖተ ካርታ እንደሆነ አንስተዋል።

ለዚህም የጋራ ትብብርን በማሳደግ መልከ ብዙ ባህሎችን ለጎብኚዎች ማቅረብ ይገባል ብለዋል።

ይህንንም እውን ለማድረግ እያንዳንዱ የቀጣናው አባል ሀገር በጋራ እና በተናጠል አቅማቸውን ሊጠቀሙ እንደሚገባም አንስተዋል።

ለዚህም የቱሪስት ስነ ምህዳራዊ ምቹነትን የሚፈጥሩ መሰረተ ልማቶችን እና የተቋማት ማሻሻያዎችን በማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል።

በምክክር መርሃ ግብሩ ላይ የኢጋድ ዋና ጸሃፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) እና የቀጣናው ሀገራት የቱሪዝም ሚኒስትሮች እየተሳተፉ ነው።

በይስማው አደራው

Exit mobile version