የሀገር ውስጥ ዜና

ፎቶን ሞተርስ ግሩፕ በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ መኪኖች አቅርቦት ዘርፍ ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት አሳየ

By Feven Bishaw

June 20, 2024

 

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 13፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የቻይናው ፎቶን ሞተርስ ግሩፕ በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ መኪኖች አቅርቦት ዘርፍ ለመሳተፍ ፍላጎት ማሳየቱ ተገለፀ፡፡

የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ዳንጌ ቦሩ ከቻይናውን ፎቶን ሞተርስ ግሩፕ ልዑክ ጋር ተወያይተዋል፡፡

አቶ ዳንጌ ÷ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በየዓመቱ በርካታ ችግኞችን ከማልማት ጎን ለጎን የኤሌክትሪክ መኪኖች አቅርቦት በማስፋት የአየር ብክለትን ለመቀነስ እየሰራች መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በዚህም ፎቶን ሞተርስ ግሩፕ ዘርፉን ለመቀላቀል መምጣቱን በደስታ የምንቀበለው ነው ማለታቸውን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

የኤሌክትሪክ መኪኖች ዘርፍን ለማበረታታት የተፈቀዱ የታክስ ማበረታቻዎችን አንስተው ፥ ግሩፑ የኤሌክትሪክ መኪኖችንና መቀያየሪያዎችን በማስገባትና በኢትዮጵያ በመገጣጠም አብሮ ቢሰራ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ ወደ መጠናቀቁ በመሆኑ ከኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት ጋር ተያይዞ ሰፊ የገበያ ፍላጎትና ይበልጥ ምቹ ሁኔታዎችን እንደሚፈጥር አስረድተዋል።

በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ መኪኖች ግብይት ዘርፍ ለመሳተፍ ከፖሊሲና ሀገራዊ ስትራቴጂ አኳያ ያሉ አስቻይ ሁኔታዎች ላይ ጥያቄ ያቀረቡት የቻይናው የፎቶን ሞተርስ ግሩፕ ስራ አስፈጻሚ ቻንግ ሩይ በሚኒስቴሩ ማብራሪያ ተሰጥቷቸዋል፡፡

ቻንግ ፎቶን ሞተርስ ግሩፕ በትራንስፖርቱ ዘርፍ ኃይል ቆጣቢና ከአካባቢ ብክለት የጸዱ መኪኖችን የሚያመርትና በዘርፉ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ምርምር የላቀ አበርክቶ ያለው መሆኑን ጠቅሰው ፥ ከሚኒስቴሩ ጋር የጀመሩትንም ግንኙነት አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።