የሀገር ውስጥ ዜና

የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የንቅናቄ መድረክ እየተካሄደ ነው

By ዮሐንስ ደርበው

June 19, 2024

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 12፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት የ2016 የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የንቅናቄ መድረክ በዓድዋ ድል መታሰቢያ እየተካሄደ ነው።

በመድረኩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የሰላም ሚኒስትር ብናልፍ አንዱዓለም፣ የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር)፣ የትምህርት ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር) እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

የ2016 የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት “በጎነትና አብሮነት ለኢትዮጵያ ከፍታ” በሚል መሪ ሐሳብ እንደሚከናወን መገለጹን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

መርሐ-ግብሩን ያዘጋጁት÷ የሰላም ሚኒስቴር፣ የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርና የትምህርት ሚኒስቴር መሆናቸው ተጠቁሟል።

የአረንጓዴ ዐሻራ፣ የማዕድ ማጋራት፣ ትምህርትና የጤና አገልግሎት፣ አቅመ ደካሞችን መደገፍ ጨምሮ በዘንድሮው መርሐ-ግብር በ14 መስኮች አገልግሎት እንደሚሰጥ ተመላክቷል፡፡

በመርሐ-ግብሩ ከ34 ሚሊየን በላይ ዜጎች እንደሚሳተፉ፤ በዚህም ከ26 ቢሊየን ብር በላይ የሚተመን አገልግሎት እንደሚሰጥ እና 50 ሚሊየን የሚጠጉ ወገኖች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ መገለጹን የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ አመላክቷል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የ2016 የክረምት ወራት በጎ ፈቃድ አገልግሎትን ማስጀመራቸው ይታወሳል።