የሀገር ውስጥ ዜና

ባንኩ ከተመዘበረበት ገንዘብ ውስጥ ያልተመለሰው 7 ሚሊየን የሚጠጋ መሆኑን አስታወቀ

By Feven Bishaw

June 14, 2024

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 7፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሲስተም ማሻሻያ ሥራ ጋር በተገናኘ መጋቢት 7 ቀን 2016 ዓ.ም ባጋጠው ችግር ያለአግባብ ከተወሰደው 801 ነጥብ 4 ሚሊየን ብር ውስጥ ያልተመለሰው 6 ነጥብ 99 ሚሊየን ብቻ መሆኑን አስታወቀ፡፡

ያለአግባብ ተመዝብሮ ከነበረው ውስጥ 794 ነጥብ 43 ሚሊየኑ መመለሱን የባንኩ መረጃ አመላክቷል፡፡

በዚህም የተመዘበረበትን ገንዘብ 99 ነጥብ 13 በመቶ የሚሆነው መመለሱን ገልጾ፤ ቀሪው 0 ነጥብ 87 በመቶ ወይም 6 ነጥብ 99 ሚሊየን ብር በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚመለስ ይጠበቃል ብሏል ባንኩ፡፡

በባንኩ የማኅበራዊ ሚዲያዎች ምስላቸው እና ስማቸው ይፋ ተደርጎ የነበሩ ግለሰቦች የሚጠበቅባቸውን ገንዘብ መክፈላቸውን እና ቀሪውን ገንዘብ በሌሎች አማራጮች ለማስከፈል ባንኩ እየተንቀሳቀሰ በመሆኑ መረጃዎቹን ከገፆቹ ላይ ማንሳቱንም አስታውቋል፡፡