የሀገር ውስጥ ዜና

ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ በኢትዮጵያ ወታደራዊ አካዳሚ ሰልጣኝ እጩ መኮንኖችን ጎበኙ

By Amele Demsew

June 02, 2024

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 25፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ በኢትዮጵያ ወታደራዊ አካዳሚ የሚገኙ ሰልጣኝ እጩ መኮንኖችን ጎበኙ።

ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ በጉብኝታችው ÷”ሀገራችንን የመሩ ታላላቅ መሪዎች በሰለጠኑበት ወታደራዊ አካዳሚ በመሠልጠናችሁ ልትኮሩ ይገባል “ሲሉ ለሰልጣኞቹ ተናግረዋል፡፡

ቀደምት የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት ይማሩ የነበሩ ሰልጣኝ እጩ መኮንኖች ፍላግ በለበሱ ማግስት የአካባቢው ወጣቶችን በማስተባበር የጣሊያንን ጦር ድል ማድረጋቸውንም አውስተዋል።

“እናተም የነሱን ፈለግ ተከትላችሁ በሀገራችሁ ላይ ሊቃጣ የሚችልን ማንኛውንም ጥቃት በብቃት መወጣት የምትችሉ ጠንካራ መሪ እንድትሆኑ ስልጠናችሁን ከወዲሁ በብቃት መወጣት ይኖርባችኋል”ነው ያሉት።

ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ በወታደራዊ አካዳሚው እየተሰሩ ያሉ የእርሻ ሥራዎችን እና ሌሎች የልማት ስራዎችንም መጎብኘታቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡