የሀገር ውስጥ ዜና

በአቪዬሽን ዘርፉ ዓለም አቀፍ ትስስርን ለማሳደግ ያለመ መድረክ እየተካሄደ ነው

By Tamrat Bishaw

May 21, 2024

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 13፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በአቪዬሽን ዘርፉ ዓለም አቀፍ ትስስርን ለማሳደግ እና በትብብር መስራት ላይ ያተኮረ 3ኛው የመጪው ዘመን አቪዬሽን ዘርፍ መድረክ በሳዑዲ ዓረቢያ-ሪያድ እየተካሄደ ነው፡፡

በመድረኩም ከ5 ሺህ በላይ በዘርፉ ያሉ የአውሮፕላን አምራቾች፣ የበረራ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት፣ የአቪዬሽን ትምህርትና ልኅቀት ማዕከላት፣ ምሁራን እንዲሁም የዘርፉ ውሳኔ ሰጪ የመንግስታትና የዓለም አቀፍ ተቋማት አመራሮች እየተሳተፉ ነው፡፡

በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) የተመራ ልዑክ ኢትዮጵያን በመወከል በዚህ ዓለም አቀፍ መድረክ ላይ እየተሳተፈ መሆኑ ተገልጿል፡፡

ልዑኩ ከፎረሙ ተሳትፎ ጎን ለጎን በሚኖሩ የሁለትዮሽ ውይይቶች ከተለያዩ አካላት ጋር እንደሚመክር ይጠበቃል መባሉን የሚኒስቴሩ መረጃ አመላክቷል፡፡

በተሳታፊ ሀገራትና ተቋማት መካከልም ከ50 በላይ የአቪዬሽን ዘርፍ ትብብሮችና የአብሮ መስራት ስምምነቶች እንደሚፈረሙ ይጠበቃል ተብሏል፡፡