አዲስ አበባ፣ መጋቢት 24፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ማሪታይም ባቦጋያ አካዳሚ ያሰለጠናቸውን የኢትዮጵያ ባሕር ኃይል አባላት አስመረቀ፡፡
ተመራቂዎቹ በስልጠናቸው ወቅት÷ ከመርከብ የሚነሳ እሳትን እንዴት መከላከል እንደሚቻል እና የእሳት አደጋ ቢነሳ እንኳ ጉዳት ሳይደርስ እንዴት መቆጣጠር እንደሚቻል ተከታትለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ባሕር ኃይል ዋና አዛዥ ተወካይ ሬር አዲሚራል ናስር አባድጋ÷ ተመራቂዎች የኢትዮጵያ ባሕር ኃይል የጀርባ አጥንት መሆናቸውን በመገንዘብ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ እንዲወጡ ማሳሰባቸውን ከመከላከያ ሠራዊት ማኅበራዊ ትስስር ገጽ ያገኘነው መረጃ አመላክቷል፡፡
የባሕር ኃይል አባል መሆንና መርከብ ላይ ግዳጅን መወጣት ጥሩ ሥነ-ምግባር፣ ወታደራዊ ዲሲፒሊን፣ ጠንካራ ግዳጅ አፈፃፀምና የሕይወት መስዋዕትነትን ጭምር እንደሚጠይቅም አስገንዝበዋል፡፡
በመሆኑም ተመራቂዎቹ በስልጠና ያገኙትን አቅም ወደ ተግባር በመለወጥ ሙያዊ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ነው በአጽርንኦት የገለጹት፡፡