Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

አትሌት ድሪባ መርጋን ጨምሮ  3 ግለሰቦች ሀሰተኛ ሰነድ አዘጋጅቶ በማቅረብ የሙስና ወንጀል ተከሰሱ

አዲስ አበባ፣ ጥር 15፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) አትሌት ድሪባ መርጋን ጨምሮ 3 ግለሰቦች ሀሰተኛ ሰነድ አዘጋጅቶ በመገልገል የሙስና ወንጀል ክስ ተመሰረተባቸው።

ክሱ የተመሰረተው በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 2ኛ የሙስና ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ነው።

ተከሳሾቹ አትሌት ድሪባ መርጋ እጅጉ በግል ስራ የሚተዳደሩት ወ/ሮ መንበረ አበበ ገብረጻዲቅ እና አቶ ስዩም አሰፋ ወንድማገኝ ናቸው።

የፍትህ ሚኒስቴር የሙስና ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ጀነራል ዐቃቤ ሕግ በተከሳሾቹ ላይ የተሳትፎ ደረጃ ጠቅሶ ተደራራቢ ክስ አቅርቦባቸዋል።

በዚህም በአንደኛው ክስ በአትሌት ድሪባ ላይ ብቻ በቀረበው ክስ የሙስና ወንጀሎችን ለመደንገግ በወጣው አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀጽ 23 ንዑስ ቁጥር 3 ስር የተመላከተውን ድንጋጌ ተላልፏል የሚል ነው።

ተከሳሹ ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለራሱ ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ 1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር በሆነውና በስራ አስኪያጅነት የሚተዳደረውን  የናይስ ሪል ስቴት ኃ/የተ/የግ/ማህበር የሆነውንና በቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 08 ስር የሚገኘውን 4 ሺህ 972 ካሬ ሜትር  ይዞታን ተመሳስለው የተዘጋጁ ሀሰተኛ ሰነዶችን ማለትም በመጋቢት 15 ቀን 2015 ዓ.ም ከሚመለከተው ተቋም እንደተሰጠ በማስመሰል የተዘጋጀ ሀሰተኛ የይዞታ ማረጋገጫ  ካርታ ለሶስተኛ ወገን ለሽያጭ ማቅረቡን ጠቅሶ ዐቃቤ ሕግ በክሱ አስፍሯል።

በተጨማሪም አትሌት ድሪባ የተባለው ተከሳሽ በውል ቁጥር 2036/2012 ዓ.ም ደግሞ በውል ሰጭ የቂርቆስ ክፍለ ከተማ መሬት ዝግጅት እና ማስተላለፍ ዘርፍ እና በውል ተቀባይ ናይስ ሪል ስቴት ኃ/የተ/የግ/ማህበር መካከል የተፈረመ በማስመሰል የተዘጋጀ ሀሰተኛ የሊዝ ውል፣ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ የተሰጠ በጥር 26 ቀን 2015 ዓ.ም በኮድ ቁጥር 2929/2929/2015 የሊዝ ውልን በማሻሻል እንደላከ በማስመሰል የተዘጋጀ ሀሰተኛ የሊዝ ውል ለሽያጭ አቅርቧል በማለት ዐቃቤ ሕግ በክሱ  አመላክቷል።

በተጨማሪም ተከሳሹ የዐቃቤ ሕግ ምስክር ውክልና ባልሰጠችበት ሁኔታ ላይ በህዳር 5 ቀን 2016 ዓ.ም ለ1ኛ ተከሳሽ ይዞታውን በሽያጭ እስከ ማስተላለፍ ድረስ እንዲያስተዳድር ውክልና እንደሰጠች ተደርጎ የተዘጋጀ ሀሰተኛ የውክልና ሰነድ ማቅረቡን በክሱ ላይ አመላክቷል።

በአጠቃላይ  1ኛ ተከሳሽ  በታህሳስ 4 ቀን 2016 ዓ.ም በይዞታው ላይ የተጠቀሱ ሀሰተኛ ሰነዶችን ትክክለኛ አስመስሎ ይዞ በማቅረብ  ይዞታውን በ700 ሚልየን ብር ለመሸጥ ሲደራደር የተያዘ መሆኑን ጠቅሶ  ዐቃቤ ሕግ በሀሰተኛ መንግስታዊ ሰነድ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ አቅርቦበታል።

በ2ኛና በ3ኛ ተከሳሾች ላይ ብቻ በቀረበው ክስ ደግሞ ተከሳሾቹ በ1996 ዓ.ም በወጣው የኢፌድሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 32 ንዑስ ቁጥር 1 (ሀ) እና የሙስና ወንጀሎችን ለመደንገግ የወጣውን አዋጅ ቁጥር 881/2007 አንቀጽ 23 ንዑስ ቁጥር 1 (ሀ) ስር የተመለከተውን ተላልፈዋል የሚል ነው።

በዚህም 2ኛ እና 3ኛ ተከሳሾች  ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለራሳቸው ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት አስበው በ1ኛ የዐቃቤ ሕግ ምስክር በሆነው እና በስራ አስኪያጅነት የሚተዳደረው ናይስ ሪል እስቴት ኃ/የተ/የግ/ማህበር ይዞታ የሆነውንና በቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 08 ስር የሚገኘውን 4 ሺህ 972 ካሬ ሜትር ይዞታ ላይ ተመሳስሎ የተሰራ ሀሰተኛ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ፣ የሊዝ ውልና የውክልና ሰነድ ያዘጋጁ መሆኑን ጠቅሶ ሀሰተኛ መንግስታዊ ሰነድ ማዘጋጀት የሙስና ወንጀል ክስ ዐቃቤ ሕግ አቅርቦባቸዋል።

3ኛ ክስ ደግሞ በ2ኛ ተከሳሽ ላይ ብቻ የቀረበ ሲሆን ይኸውም የወንጀል ሕግ አንቀጽ 390 ንዑስ ቁጥር 1 ስር የተመለከተውን መተላለፍ  የሚል ክስ ቀርቦባታል።

በዚህም በታህሳስ 4 ቀን በ 2016 ዓ.ም በኮልፌ ቀራንዮ ክ/ከተማ ወረዳ 08 ልዩ ቦታው አረንጓዴ ሰፈር ተብሎ ከሚታወቀው ቦታ አካባቢ በሚገኘው የስራ ቦታዋ ውስጥ በፍርድ ቤት ትእዛዝ መሰረት በተደረገ ብርበራ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ በልደታ ክ/ከተማ ትምህርትና ስልጠና ጽ/ቤት የዕውቀት ለህብረት የ2ኛ ደረጃ ት/ቤት የተማሪዎች ካርድ እና በትምህርት ሚኒስቴር አባይ የመጀመርያ ደረጃ ት/ቤት የተማሪ ውጤት መግለጫ ካርድ የተገኘባት በመሆኑ የሐሰት ስራ ለመፈጸም የሚያገለግሉ መሳርያዎችና መስርያዎች ይዞ መገኘት ወንጀል ተከሳለች።

በዚህ መልኩ የቀረበባቸው ክስ ዝርዝር በችሎት እንዲደርሳቸው ተደርጓል።

በታሪክ አዱኛ

Exit mobile version