የሀገር ውስጥ ዜና

አንጎላ ከኢትዮጵያ ጋር በግብርናው ዘርፍ በትብብር መሥራት እንደምትፈልግ ገለጸች

By ዮሐንስ ደርበው

November 28, 2023

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 18፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በግብርናው ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር መሥራት እንደሚፈልጉ የአንጎላ ፕሬዚዳንት ጆአዎ ማኑዌል ጎንካልቬስ ሎሬንኮ ገለጹ፡፡

በአንጎላ የኢትዮጵያ አምባሳደር ፍርቱና ዲበኩ የሹመት ደብዳቤያቸውን ለአንጎላ ፕሬዚዳንት ጆአዎ ማኑዌል ጎንካልቬስ ሎሬንኮ አቅርበዋል ።

በዚሁ ወቅትም ኢትዮጵያ በንግድ፣ በግብርና፣ በቱሪዝም እና በኢንቨስትመንት ዘርፎች ከአንጎላ ሪፐብሊክ ጋር በቅርበት መሥራት እንደምትፈልግ አምባሳደር ፍርቱና ገልፀዋል።

ፕሬዚዳንት ጆአዎ ማኑዌል ጎንካልቬስ ሎሬንኮ በበኩላቸው÷ ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በግብርናው ዘርፍ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበች እንደምትገኝ አንስተዋል፡፡

አንጎላም ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር መሥራት እንደምትፈልግ መናገራቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡

በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ድርድር ዙሪያም÷ ኢትዮጵያ ሥምምነቱን ከታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ጋር በአፍሪካ ኀብረት ማዕቀፍ ስር ችግሮች እንዲቀረፉ እየሠራች እንደምትገኝ ተገልጿል፡፡