አዲስ አበባ፣ ሕዳር 18፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በግብርናው ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር መሥራት እንደሚፈልጉ የአንጎላ ፕሬዚዳንት ጆአዎ ማኑዌል ጎንካልቬስ ሎሬንኮ ገለጹ፡፡
በአንጎላ የኢትዮጵያ አምባሳደር ፍርቱና ዲበኩ የሹመት ደብዳቤያቸውን ለአንጎላ ፕሬዚዳንት ጆአዎ ማኑዌል ጎንካልቬስ ሎሬንኮ አቅርበዋል ።
በዚሁ ወቅትም ኢትዮጵያ በንግድ፣ በግብርና፣ በቱሪዝም እና በኢንቨስትመንት ዘርፎች ከአንጎላ ሪፐብሊክ ጋር በቅርበት መሥራት እንደምትፈልግ አምባሳደር ፍርቱና ገልፀዋል።
ፕሬዚዳንት ጆአዎ ማኑዌል ጎንካልቬስ ሎሬንኮ በበኩላቸው÷ ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በግብርናው ዘርፍ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበች እንደምትገኝ አንስተዋል፡፡
አንጎላም ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር መሥራት እንደምትፈልግ መናገራቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡
በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ድርድር ዙሪያም÷ ኢትዮጵያ ሥምምነቱን ከታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ጋር በአፍሪካ ኀብረት ማዕቀፍ ስር ችግሮች እንዲቀረፉ እየሠራች እንደምትገኝ ተገልጿል፡፡