ዓለምአቀፋዊ ዜና

ሃማስ ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ሥምምነቱ እንዲራዘም ጠየቀ

By Alemayehu Geremew

November 27, 2023

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 17፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ሃማስ ዛሬ የሚያበቃው የአራቱ ቀናት ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ሥምምነት እንዲራዘም ፍላጎት እንዳለው አስታወቀ፡፡

ሃማስ እንዳስታወቀው÷ ምንም እንኳን ታጋቾቹን በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ለማስለቀቅ ጥረት ቢያደርግም ካለው የጊዜ መጣበብ አንጻር ማሳካት አልቻለም፡፡

የተኩስ አቁም ሥምምነቱ ለተጨማሪ ከሁለት እስከ አራት ቀናት እንዲራዘም ፍላጎት ያለው ሃማስ፤ ይህንን ፍላጎቱን ለአሸማጋዮቹ ኳታር እና ግብፅ አስረድቷል ተብሏል፡፡

ካሳለፍነው አርብ ጀምሮ ሥራ ላይ በዋለው የአራቱ ቀናት የተኩስ አቁም ሥምምነት÷ ሃማስ 40 እስራዔላውያንን እና 18 የውጭ ሀገር ዜጎችን ከእገታ ሲለቅ እስራዔል በበኩሏ 117 ፍልሥጤማውያንን መፍታቷን የቲ አር ቲ መረጃ ያመላክታል።