ናይጄሪያና አንጎላ “ኦፔክ” ፕላስ ያስቀመጠውን የወጪ የነዳጅ ምርት ቅነሳ ተቃወሙ

By Alemayehu Geremew

November 25, 2023

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 14፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የነዳጅ ላኪ ሀገራት ቡድን (ኦፔክ ፕላስ) አባል የሆኑት ናይጄሪያና አንጎላ ቡድኑ ያስቀመጠውን የወጪ የነዳጅ ምርት የመቀነስ ዕቅድ ተቃወሙ፡፡

ቡድኑ ለወጪ ንግድ የሚያመርቱትን የነዳጅ አቅርቦት ድርሻም እንዲጨምርላቸው ጠይቀዋል ነው የተባለው፡፡

ይህን ተከትሎ በአባል ሀገራቱ መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ተጨማሪ የወጪ ምርት ቅነሳ ላይ ለመወያየት የቀጠሩትን ጊዜ ለማራዘም እንዳስገደዳቸው አር ቲ ዘግቧል፡፡

ሀገራቱ ቀደም ሲል በወጪ የነዳጅ አቅርቦት ቅነሳ ላይ የደረሱበት ሥምምነት የዓለም የነዳጅ ዋጋ እንዲንር ማድረጉን ምንጩ ሬውተርስን ዋቢ አድርጎ አስታውሷል፡፡

የነዳጅ ላኪ ሀገራት ቡድን (ኦፔክ) ፕላስ ÷ ሥብሰባ መራዘምን ተከትሎ ደግሞ ግዙፎቹ የምዕራብ ቴክሳስ እና የአትላንቲክ ድፍድፍ ነዳጅ አቅራቢዎች የመሸጫ ዋጋ ላይም ቅናሽ መታየቱ ነው የተገለጸው፡፡