የሀገር ውስጥ ዜና

በኦሮሚያ ክልል 2 ነጥብ 9 ሚሊየን የመማሪያ መጽሐፍት መሰራጨቱ ተነገረ

By Amele Demsew

November 09, 2023

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 29፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በኦሮሚያ ክልል 2 ነጥብ 9 ሚሊየን የአዲሱ ስርዓተ ትምህርት የመማሪያ መጽሐፍት ለሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መሰራጨቱን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ፡፡

የቢሮው አማካሪ ኤፍሬም ተሰማ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደገለጹት÷ ከትምህርት ሚኒስቴር ለክልሉ የደረሰውን መጽሐፍ ለዞኖችና ከተማ አስተዳደሮች ተከፋፍሎ ለትምህርት ቤቶች እንዲሰራጭ ተደርጓል።

የክልሉ የመማሪያ መጽሐፍት ፍላጎት 8 ሚሊየን ቢሆንም ከሚኒስቴሩ በመጀመሪያው ዙር 2 ነጥብ 9 ሚሊየን መጽሐፍ ብቻ ደርሶናል ነው ያሉት።

ለችግሩ አፋጣኝ መፍትሔ ለመስጠት በሁሉም ትምህርት ቤቶች በሚገኙ ቤተመጽሐፍት በሶፍት ኮፒ እንዲሰራጭ እና ስማርት ስልክ ያላቸው መምህራን ለተማሪዎች እና ወላጆች እንዲያዳርሱ መደረጉንም ገልጸዋል።

በክልሉ የሚገኙ ባለሃብቶች፣ መንግስታዊ እና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም የመጽሐፉን ቅጂ አሳትመው እንዲያሰራጩ መመሪያ ተሰጥቷል ብለዋል አቶ ኤፍሬም።

በመሳፍንት እያዩ