ዓለምአቀፋዊ ዜና

የተመድ የሥራ ኃላፊ በ72 ሠዓታት ኒጀርን ለቀው እንዲወጡ ታዘዙ

By Alemayehu Geremew

October 11, 2023

አዲስ አበባ፣ መስከረም 30፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በኒጀር የሚገኙት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የሥራ ኃላፊ በ72 ሰዓታት ውስጥ ኒጀርን ለቀው እንዲወጡ በመፈንቅለ መንግስት ሥልጣኑን የተቆጣጠረው የሀገሪቱ ወታደራዊ አሥተዳደር ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡

አሥተዳደሩ ትዕዛዙን ሲያስተላልፍ የሚያሳይ ምሥል በዛሬው ዕለት በኤኤፍፒ መተላለፉን ቫንጋርድ ዘግቧል፡፡

በወታደራዊ አሥተዳደሩ የሚመራው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ÷ በኒጀር የሚገኙት የተመድ የሰብዓዊ ዕርዳታ አሥተባባሪ ሉዊዝ ኦቢን በ72 ሰዓታት ጊዜ ውስጥ የኒጀርን መዲና በአስቸኳይ ለቀው እንዲወጡ አዟል።

በኒጀር ያለውን አለመረጋጋት ወደ ሠላማዊ ሁኔታ ለመመለስ የሚደረገው ጥረት ዕውን እንዳይሆን አስተባባሪው እንቅፋት እንደሆኑበት በመግለጽ አስተዳደሩ ወንጅሏቸዋል።

አስተዳደሩ ቀደም ብሎ በሀገሪቷ የሚገኙት የፈረንሳይ ወታደሮች በአስቸኳይ እንዲወጡ ባስተላለፈው ትዕዛዝ መሰረት 1 ሺህ 400 ያህሉ ወታደሮች ጠቅልለው መውጣታቸው ይታወቃል።