አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 7፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መንግስት ያለአግባብ ሊያጣው የነበረ 2 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ማዳን መቻሉን የከተማዋ ፍትሕ ቢሮ አስታውቋል፡፡
በቢሮው የሕግ ክትትል ዘርፍ ም/ሃላፊ አቶ ተስፋዬ ደጀኔ እንደገለጹት÷በ2015 በጀት ዓመት በመዲናዋ የተከሰቱ ብልሹ እና ሕገ ወጥ ተግባራትን ከመቅረፍ አንጻር በርካታ ስራዎች ተከናውነዋል፡፡
በከተማ አስተዳደሩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 7 ሺህ 499 ክሶች እና የፍርድ ቤት ክርክሮች እንደነበሩ አቶ ተስፋዬ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ውስጥም ቢሮው 2 ሺህ 497 መዝገቦችን በመከራከር በፍርድ ቤት ውሳኔ እንዲያገኙ ማድረጉን ነው የገለጹት፡፡
2 ሺ 266 መዝገቦች ለመንግስት እንዲወሰኑ ተደርጓል ያሉት ም/ሃላፊው÷ በዚህም መንግስት ሊያጣው የነበረ 2 ነጥብ 58 ቢሊየን ብር በላይ ማዳን ተቸሏል ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል አምስት ትልልቅ ክርክሮችን በድርድር እንዲያልቁ በማድረግ መንግስት ያለአግባብ ሊያጣው የነበረ 299 ሚሊየን ብር ማዳን መቻሉን ጠቁመዋል፡፡
በመላኩ ገድፍ