የሀገር ውስጥ ዜና

በኮንትሮባንድ የገቡ የተለያዩ ሞባይል ስልኮች እና የብር ጌጣጌጦች ተያዙ

By Melaku Gedif

June 23, 2023

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 16፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በኮንትሮባንድ የገቡ የተለያዩ ሞባይል ስልኮች እና የብር ጌጣጌጦች መያዙን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡

የኮንትሮባንድ እቃዎቹ በአዲስ ከተማ ክ/ከተማ ወረዳ 8 ልዩ ቦታው አዲስ አበባ የገበያ ማዕከል አካባቢ ነው ከሕብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማ  የተያዙት፡፡

በዚህም ምንም ዓይነት ቀረጥ ሳይከፈልባቸው በኮንትሮባንድ ወደ ሀገር ውስጥ የገቡና በስድስት ካርቶን የታሸጉ የተለያዩ ጌጣጌጦችና ብዛታቸው 970 የሚሆኑ የሞባይል ስልኮች መያዛቸው ተገልጿል፡፡

ፖሊስ በዚህ ድርጊት ተሳታፊ የሆነ ተጠርጣሪንም ከእነ ኤግዚቢቱ በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ እያጣራ  እንደሚገኝም ተመላክቷል፡፡