የሀገር ውስጥ ዜና

በሐረሪ ክልል በትራፊክ አደጋ የ6 ሰዎች ሕይወት አለፈ

By Alemayehu Geremew

May 29, 2023

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 21፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በሐረሪ ክልል በደረሰ የትራፊክ አደጋ የሥድስት ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተገለጸ፡፡

ግንቦት 20 ቀን 2015 ዓ.ም ከምሽቱ አራት ሠዓት ሲሆን ከአወዳይ ወደ ጅጅጋ ሲጓዝ የነበረ አይሱዙ የጭነት ተሽከርካሪ በሐረሪ ክልል ሶፊ ወረዳ ቂሌ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር ልዩ ሥፍራው ገንደ ሀጆ ተብሎ በሚጠራ ቦታ ሰርገኛ አጅበው ሲሄዱ የነበሩ ሥድስት ሰዎችን ገጭቶ ሕይወታቸው ማለፉን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታውቋል።

ከሟቾቹ በተጨማሪ በሥምንት ሰዎች ላይ ከባድና ቀላል የአካል ጉዳት አድርሶ ተሽከርካሪው መገልበጡን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አደጋ መርማሪ ዋና ሳጅን ረስተም መዘር ገልጸዋል።

በአደጋው ጉዳት የደረሰባቸው ÷ በሐረር ሕይወት ፋና ሆስፒታል የሕክምና እርዳታ እየተደረገላቸው መሆኑን መርማሪው ጨምረው ተናግረዋል፡፡

የአደጋው መንሥዔ እየተጣራ መሆኑንም ከኮሚሽኑ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡