አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 27፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ባለፉት ዘጠኝ ወራት 1 ሺህ 80 አዳዲስ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታቸው መጠናቀቁን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር አስታወቀ።
የዘርፉ የዘጠኝ ወራት እቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ነው።
የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አይሻ መሃመድ(ኢ/ር) እንደገለጹት÷ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተከናወኑ የመስኖና አርብቶ አደር አካባቢ ፕሮጀክቶች አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል።
ከተከናወኑት ተግባራት መካከል 1 ሺህ 80 የሚደርሱ አዳዲስ የመስኖ ፕሮጀክቶች መጠናቀቃቸውን ገልጸዋል፡፡
በአዳዲሶቹ የመስኖ ፕሮጀክቶች 251 ሺህ 500 በላይ ሄክታር መሬት ማልማት እንደተቻለ ጠቅሰው÷ በዚህም ከ315 ሺህ 400 በላይ ቤተሰቦችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ነው ያሉት።
ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የተለያዩ የልማት ስራዎች መሰራታቸውን የገለጹት ሚኒስትሯ÷ መለስተኛና አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶችም ጥገና እንደተደረገላቸው አንስተዋል።
በድርቅና በጎርፍ ተጎጂ በሆኑ አርብቶ አደር አካባቢዎች ምላሽ መስጠት የሚያስችሉ ስራዎች እንደተከናወኑ መናገራቸውንም ኢዜአ ዘግቧል፡፡