የሀገር ውስጥ ዜና

8ተኛው የአለም የትብብር ኢንዱስትሪዎች ፎረም ተጀመረ

By Shambel Mihret

March 21, 2023

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 12፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) 8ኛው የአለም የትብብር ኢንዱስትሪዎች ፎረም በቱርክ ኢስታንቡል መካሄድ ጀምሯል፡፡

የፎረሙ ዋና አላማ በቱርክና በአፍሪካ ነጋዴዎች መካከል ያለውን ትብብር ለማሳደግ እና የቱርክ መካከለኛና አነስተኛ  ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች ምርቶችን ማስተዋወቅ መሆኑ ተመላክቷል፡፡

ከ54 አገሮች የተውጣጡ ተጋባዥ የኩባንያ ባለቤቶች እና ከ400 በላይ የቱርክ ኩባንያዎች ምርቶቻቸዉን ያቀረቡ ሲሆን÷ ከ1 ሺህ 500 በላይ ተሳታፊዎች በፎረሙ እየተሳተፉ እንደሚገኝ ከቱርክ የኢትዮጵያ ኤንባሲ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

በፎረሙ ላይ ከኢትዮጵያም ወደ 20 የሚጠጉ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች፣ አስመጪና ላኪ ድርጅቶች የተሳተፉ ሲሆን÷ ከቱርክ አቻዎቻቸው ጋር ተወያይተዋል።

ፎረሙ እስከ ነገ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡