የሀገር ውስጥ ዜና

የሰፈነውን ሠላም ተከትሎ ወደ መደበኛ ሥራችን ገብተናል – የትግራይ ክልል አርሶ አደሮች

By Alemayehu Geremew

March 03, 2023

አዲስ አበባ፣ የካቲት 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የሰፈነው አንፃራዊ ሠላም ወደ መደበኛ ሥራችን እንድንመለስ አድርጎናል ሲሉ በሰሜን ምዕራብ ትግራይ ዞን የታኅታይ ቆራሮ ወረዳ አርሶ አደሮች ተናገሩ፡፡

መንግሥት የግብርና ግብዓት እንዲያቀርብላቸውም አርሶ አደሮቹ ጠይቀዋል።

የወረዳው ግብርና ጽሕፈት ቤት የመስኖ ሥራ አስተባባሪ ኢዮብ ገብረ መድኅን እንደገለጹት ÷ በወረዳው 1 ሺህ 100 ሄክታር በበጋ መስኖ እየለማ ነው፡፡

የማዳበሪያ፣ የምርጥ ዘርና የነዳጅ አቅርቦት ችግር መኖሩን ገልጸው÷ በዚህም አርሶ አደሮች ሥራቸውን ለማሳለጥ በጥቁር ገበያ እስከ መገበያየት ደርሰዋል ነው ያሉት፡፡

እስካሁንም የጓሮ አትክልት፣ በቆሎ፣ ሽምብራ፣ ሽንኩርትና መሰል ምርቶችን አርሶ አደሮቹ በመስኖ እያለሙ ስለመሆኑ አስረድተዋል፡፡

በአካባው የፌደራል መንግስት የሰላምና ፀጥታ ማስተባበር ቡድን አባል ታከለ ቶሎሳ÷ የግብዓት አቅርቦት ችግሮችን ለመፍታት ከባለድርሻ አካላት እየተሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

በአፈወርቅ እያዩ