Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

ለታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ከ867 ሚሊየን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ

አዲስ አበባ፣ ጥር 30፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ባለፋት ሥድሥት ወራት ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ከ867 ሚሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብስቡን የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት ገለጸ።
 
የጽህፈት ቤቱ የሕዝብ ግንኝነት ዳይሬክተር አቶ ኃይሉ አብርሃም እንደገለጹት÷ ሕዝቡ ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የሚያደርገው አስተዋጽኦ አጠናክሮ ቀጥሏል።
 
ሕዝቡ ለግድቡ ግንባታ የገንዘብ ድጋፍን ጨምሮ የተለያየ አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ዳይሬክተሩ አንስተዋል፡፡
 
በተያዘው በጀት ዓመት በመጀመሪያው ስድስት ወራት 1 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ÷ ከ867 ሚሊየን ብር በላይ መሰብሰብ መቻሉን ጠቁመዋል።
 
የተሰበሰበው ገንዘብ ከዳያስፖራው፣ ከሀገር ውስጥ የቦንድ ግዥና ስጦታ እንዲሁም ከ8100 A አጭር የጽሁፍ መልዕክት መሆኑንም ነው የተናገሩት።
 
በተለይም ደግሞ የቦንድ ግዥና ስጦታ ከተሰበሰበው ገቢ ውስጥ ትልቁን ድርሻ መያዛቸውን ተናግረዋል።
 
ጽህፈት ቤቱ አዳዲስና ነባር የገቢ ማሰባሰቢያ ዘዴዎችን በመተግበር የድጋፍ ማሰባሰብ ስራውን እንደሚያጠናክር ነው የገለጹት።
 
ሕብረተሰቡ ለግድቡ ግንባታ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥልም አቶ ኃይሉ ጥሪ ማቅረባቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
Exit mobile version