የሀገር ውስጥ ዜና

በደቡብ ወሎ ዞን 100 የመጠጥ ውኃ ተቋማት ተጠግነው ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ

By ዮሐንስ ደርበው

January 03, 2023

አዲስ አበባ፣ ታኅሣሥ 25፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በደቡብ ወሎ ዞን በተለያየ ምክንያት ጉዳት የደረሰባቸው 100 የመጠጥ ውሃ ተቋማት በ40 ሚሊየን ብር ተጠግነው ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ፡፡

የዞኑ ውኃና ኢነርጂ መምሪያ የመጠጥ ውኃ ግንባታና ጥገና ባለሙያ አቶ ንጉስ ተፈራ እንደገለጹት÷ ተጠግነው ለአገልግሎት በበቁት የውኃ ተቋማት 72 ሺህ ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል፡፡

የንፁህ መጠጥ ውኃ ተቋማቱን መልሶ ለመጠገን 40 ሚሊየን ብር ወጪ መደረጉን ለኢዜአ ተናግረዋል፡፡

በተያዘው ዓመት 180 አነስተኛና መካከለኛ የመጠጥ ውኃ ተቋማትን በአዲስ የመገንባት ሥራ መጀመሩን እና ለግንባታው 82 ሚሊየን ብር በጀት መያዙን ገልጸዋል፡፡

ግንባታቸውም እስከ መጪው ግንቦት ወር መጨረሻ ድረስ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት እንደሚሆኑ ይጠበቃል ብለዋል፡፡

የውኃ ተቋማቱ ተጠናቀው ለአገልግሎት ሲበቁ 48 ሺህ ሰዎችን የንጹህ መጠጥ ውኃ ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚያስችሉ ጠቁመዋል፡፡

የደቡብ ወሎ ዞን የመጠጥ ውኃ ሽፋን 54 በመቶ መሆኑ ተመላክቷል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!