Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

አገልግሎቱ ለአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ከ1 ሺህ በላይ መጻሕፍትን አበረከተ

አዲስ አበባ ፣ ሕዳር 2 ፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ለአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ከአንድ ሺህ በላይ መጻሕፍትን አበርክቷል፡፡

መጻሕፍቶቹን የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር ተስፋሁን ጎበዛይ ለአብርሆት ቤተ መጻሕፍት የበላይ ጠባቂ ኢንጅነር ውባየሁ ማሞ አስረክበዋል፡፡

ዋና ዳይሬክተሩ ተስፋሁን ጎበዛይ እንዳሉት÷ መጻሕፍቶቹ በብዛት ገበያ ላይ የማይገኙ፣ ለጥናታዊ ጽሁፍ የሚያገለግሉና ትምህርታዊ ይዘት ያላቸው ናቸው።

በተጨማሪም በተለያዩ ደራሲዎች የተጻፉ ልቦለድና ታሪካዊ መጽሐፍቶችንም መለገሳቸውን ጠቅሰዋል።

የአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት የበላይ ጠባቂ ኢንጅነር ውባየሁ ማሞ በበኩላቸው÷በተማረ ሃይል የታነጸች ሀገር ለመገንባት አንባቢ ትውልድ መፍጠር ያስፈልጋል ብለዋል።

መጽሐፍትን በመለገስ የነገ አገር ተረካቢ ትውልድ የተሻለ እውቀት እንዲገበይ ማድረግ ይቻላልም ነው ያሉት።

የአብርሆት ቤተመጻሕፍትን ለማደራጀት መፀሐፍትን ከማሰባሰብ አንፃር እስካሁን እየተሰሩ ያሉት ተግባራት በጥሩ ሁኔታ እየተካሔዱ እንደሆነ መግለጻቸውንም ኢዜአ ዘግቧል፡፡

Exit mobile version