የሀገር ውስጥ ዜና

አፍሪካውያን ወጣቶች የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል የአህጉሪቷ አምባሳደር ሆነው ሊሰሩ ይገባል – ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ

By Amele Demsew

November 08, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 29፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) አፍሪካውያን ወጣቶች የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ የአህጉሪቷ አምባሳደር ሆነው ሊሰሩ ይገባል ሲሉ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ ተናገሩ፡፡

“ወጣቶችን በአድቮኬሲ ስራዎች በማሳተፍ የአየር ንብረት ለውጥ ችግሮችን በዘላቂነት መቅረፍ” በሚል መሪ ሃሳብ ለሁለት ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የሞዴል አፍሪካ ህብረት የወጣቶች ጉባኤ ተጠናቋል።

በጉባኤውም ከተለያዩ አፍሪካ ሀገራት የመጡ ወጣቶች ተሳትፈዋል፡፡

በጉባኤው ማጠናቀቂያ መርሐ ግብር ላይ ንግግር ያደረጉት የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትሯ ፥ የአየር ንብረት ለውጥ የዓለማችን የወቅቱ ፈተና መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በተለይ አፍሪካውያን በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ ለበርካታ የተፈጥሮ አደጋዎች ተጋላጭ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

ከዚህ አኳያ ችግሩን በትብብር መመከት እንደሚገባ ጠቅሰው ፥ ለዚህ ደግሞ የወጣቶች ተሳትፎ ወሳኝ ሚና እንዳለው አስገንዝበዋል፡፡

አፍሪካውያን ወጣቶች የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ የአህጉሪቷ አምባሳደር ሆነው ሊሰሩ ይገባል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡