Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት አመራሮች በደቡብ ክልል በኩታ ገጠም እየለማ የሚገኝን ማሳ ጎበኙ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 16፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ሀገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት አመራሮች በደቡብ ክልል በጉራጌ ዞን ሶዶ ወረዳ በኩታ ገጠም እየለማ የሚገኝን የስንዴ፣ ባቄላና ጤፍ ማሳን ጎበኙ፡፡

በጉብኝቱ ላይ÷ የምክር ቤቱን ሰብሳቢ መብራቱ መለሰን ጨምሮ በደቡብ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪ እና የግብርና ቢሮ ኃላፊ ኡስማን ሱሩር እና የሁሉም የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካዮች ተገኝተዋል።

በሶዶ ወረዳ በተለያዩ ሰብሎች ከተሸፈነው ከ49 ሺህ ሔክታር በላይ ማሳ ውስጥ÷ 80 በመቶው በኩታ ገጠም የለማ መሆኑ ተገልጿል፡፡

60 በመቶ ያህሉ በሜካናይዜሽን ታግዞ የለማ መሆኑን የደቡብ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት መረጃ ያመላክታል፡፡

አቶ ኡስማን ሱሩር ባደረጉት ገለጻ÷ የፖለቲካ ፓርቲዎች የተለየ አቋም ቢኖራቸውም በእንዲህ ዓይነቱ የዜጎችን ሕይወት የሚቀይር ተግባር ላይ ያለልዩነት መቆም አለባቸው ብለዋል ።

ዶክተር መብራቱ መለሰ በበኩላቸው÷ በደቡብ ክልል ያለው የግብርና ልማት ሥራ ግብርናው በትክክል ከተመራ የኢኮኖሚው የጀርባ አጥንት መሆኑ በተጨባጭ የታየበት ነው ብለዋል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

Exit mobile version