የሀገር ውስጥ ዜና

በአሸባሪው ህወሓት ሊዘረፍ የነበረን የፀደይ ባንክ ገንዘብ መሬት ቆፍረው በመቅበር ያዳኑት አባትና ልጅ

By Amele Demsew

October 25, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 15፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በዛሪማ ከተማ በህወሓት የሽብር ቡድን ሊዘረፍ የነበረን የፀደይ ባንክ ገንዘብ መሬት ቆፍረው በመቅበር አባትና ልጅ መታደጋቸው ተሰምቷል።

የሽብር ቡድኑ ሐምሌ 18 ቀን 2013 ዓ.ም የዛሪማ ከተማን በወረረ ወቅት የወቅቱ አብቁተ የአሁኑ ፀደይ ባንክ ሰራተኛ የነበረው አቶ ደጀን ጀጃው ነፍሱን ለማዳን በመሮጥ ፋንታ የህዝብ ገንዘብ ለሽብር ቡድኑ ጥየ አልወጣም ብሎ ይወስናል፡፡

በዚህም ሁለት ጥበቃዎችን በማስተባበር በተቋሙ ዋና ቅርጫፍ ቢሮ የነበረን 195 ሺህ ብር ከቢሮ ካዝና ሰብሮ በማውጣት ወደአባቱ ቤት ከአንድ ቀን በላይ የሚሆን የእግር ጉዞ በመጓዝ ያደርሰዋል።

የጎንደር ቅርንጫፍ ስራ አስኪያጅ አቶ ተሸመ ሞላ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት፥ ልጅ ከአባቱ አቶ ጀጃው እንደሻው ጋር በመነጋገር የወሰደውን ገንዘብ መሬት ቆፍሮ ከቀበረ በኋላ ለእርሳቸው በመደወል ብሩ ያለበትን ቦታ አሳውቆኛል ብለዋል፡፡

ወደዘመቻ ስለምሄድ ምናልባት የህይወት መስዋዕትነት ከከፈልኩ በሚል፥ ከአባቱ አልያም ከአያቱ እጅ እንዲረከቡ እንደነገራቸው ስራ አስኪያጁ ያስታውሳሉ።

የህወሓት የሽብር ቡድን መስከረም 5 ቀን ዛሪማ ከተማን ለቆ ሲወጣ በድጋሚ ለስራ አስኪያጁ በመደወል ፥ ተቋሙ መኪና ልኮ ብሩን እንዲረከበው አድርጎ የህዝብ ንብረት ከዘረፋና ወረራ እንዲድን ማድረጉንም ነው የሰማነው፡፡

ፀደይ ባንክ በዚያ ህወሓት ከተማዋን በከባድ መሳሪያ በሚደበድብበት ወቅት ይህንን የደጀንነት እና የጀግንነት ተግባር ለፈፀሙት አባትና ልጅ ማበረታቻ እና የክብር እውቅና ምስክር ወረቀት ሠጥቷቸዋል።

በኤልያስ አንሙት