የሀገር ውስጥ ዜና

የሶማሊያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሀምዛ አብዲ በባህርዳር የልማት ተቋማትን ጎበኙ

By Feven Bishaw

October 16, 2022

 

አዲስ አበባ ፣ ጥቅምት 6 ፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የሶማሊያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሀምዛ አብዲ እና ልዑካቸው ከአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል ከፋለ ጋር በባህር ዳር የሚገኙ የልማት ተቋማትን ጎብኝተዋል፡፡

በጉብኝታቸውም ከ1 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ በመገንባት ላይ የሚገኘውን የዓባይ ተለዋጭ አዲስ ድልድይን ጨምሮ የዓባይ ወንዝ፣ የጣና እና የከተማዋን ገጽታ ተመልክተዋል።

በተጨማሪም በጣና ኃይቅ ካሉ ገዳማት አንዷ የሆነችውን ደብር ማሪያም፣ ዓባይ ከጣና ጋር የሚገናኝበት “ዓባይ እራስ” የተባሉ ቦታዎችንም ጎብኝተዋል።

የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ እያካሄደ የሚገኘውን የአረንጓዴ ልማት እና የዓውደ-ግቢ ማስዋብ ስራንም ጎብኝተዋል፡፡

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶክተር ፍሬው ተገኝ ÷ ለሶማሊያውያን ዜጎች ነፃ የትምህርት ዕድል ለመስጠት ቃል ገብተዋል።

ዩኒቨርሲቲው ከምስራቅ አፍሪካ የመጡ ተማሪዎችን በተለያዩ ደረጃዎች እያስተማረ እንደሚገኝና 200 ከሚሆኑ ተባባሪ አካላት ጋርም እየሰራ መሆኑን አንስተዋል፡፡