Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

በሶማሌ ክልል ከ4 ሺህ በላይ የነዳጅ ድጎማ ተጠቃሚ ተሽከርካሪዎች ተመዘገቡ

አዲስ አበባ፣ መስከረም 4፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በሶማሌ ክልል የነዳጅ ድጎማ ተጠቃሚ የሚሆኑ ከአራት ሺህ በላይ ተሽከርካሪዎች ምዝገባ መከናወኑን የክልሉ የንግድና ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ፡፡

በክልሉ ከ3 ሺህ በላይ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ተሽከርካሪዎችም የነዳጅ ድጎማ አሰራር ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸው ነው የተገለጸው፡፡

የነዳጅ ድጎማው ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች አገልግሎት የሚሰጡ 3 ሺህ 375 የሚሆኑ በታሪፍ እና በስምሪት ቁጥጥር ላይ የተመሠረተ መለስተኛ፣ መካከለኛ የብዙኃን ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ተሽከርካሪዎች መጠቀም መቻላቸው ተገልጿል፡፡

በክልሉ በተመረጡ 91 ማደያዎች ባለሀብቶችና ለህዝብ አገልግሎት የሚሰጡ አሽከርካሪዎች በቴሌ ብር እየተከናወነ የሚገኘውን የነዳጅ ክፍያ ስርዓት አፈጻጸም በቂ ግንዛቤ እንዲኖራቸው እየተሰራ መሆኑም ተጠቅሷል፡፡

በቴሌ ብር አማካኝነት በ60 ቀናት ውስጥ 53 ሺህ ተሽከርካሪዎች በድጎማው ተጠቃሚ መሆናቸውንና በዚህም ከ1 ቢሊየን ብር በላይ ግብይት መፈጸሙን የኢትዮ ቴሌኮም ሞባይል ገንዘብ ዲቪዢን ዋና ኃላፊ አቶ ብሩክ አዳነ ገልጸዋል።

በቴክኖሎጂ ክፍያ ስርዓቱ ላይ የሚታየውን የግንዛቤ እጥረት ለመቅረፍ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በጋራ እየተሰራ እንደሚገኝ ቢሮው ማስታወቁን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

Exit mobile version