የሀገር ውስጥ ዜና

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የተፈናቀሉ ወገኖች ወደቀያቸው እየተመለሱ ነው- አቶ አሻድሊ ሀሰን

By Shambel Mihret

September 01, 2022

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 26፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አንፃራዊ ሰላም እየሰፈነ መምጣቱን ተከትሎ የተፈናቀሉ ወገኖች ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ እየተደረገ መሆኑን አቶ አሻድሊ ሀሰን ገለጹ፡፡

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን ከዓለም አቀፍ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ተወካዮች ጋር ክልሉ እየሰራ ያለውን የመልሶ ግንባታ ስራ በሚደግፉበት ሁኔታ ላይ መክረዋል፡፡

የክልሉን ነባራዊ ሁኔታ አስመልክቶ ማብራሪያ የሰጡት አቶ አሻድሊ÷  ክልሉ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በገጠመው የጸጥታ ችግር በርካቶች ከመኖሪያ ቀያቸው መፈናቀላቸውን እና ቤት ንብረታቸው መውደሙን ገልጸዋል፡፡

ትምህርት ቤቶች፣  የጤና እና የውሃ ተቋማት መውደማቸውን ጠቅሰው÷ አሁን ላይ በክልሉ አንፃራዊ ሰላም እየሰፈነ መምጣቱን ተከትሎ የተፈናቀሉ ወገኖች ወደ ቀድሞ ቦታቸው  እንዲመለሱ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡

የወደሙ ተቋማትን መልሶ ለመገንባትና ተፈናቃዮችን ለማቋቋም በመንግስት አቅም ብቻ የሚቻል ባለመሆኑ፥  የአጋር አካላት ድጋፍ ያስፈልጋልም ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፡፡

የዓለም አቀፍ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ተወካዮች በበኩላቸው÷ በቀጣይ በጊዜያዊ መጠለያ፣ በትምህርት፣ በጤና እና በውሃ ስራዎች ላይ  ድጋፍ ለማድረግ ቃል መግባታቸውን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ  ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡