አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 13፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ሶማሊላንድ ቢቢሲ የግዛቴን ሉዓላዊነት ተጋፍቷል በሚል ሥራውን እንዲያቆም መወሰኗን አስታወቀች፡፡
የሶማሊላንድ ማስታወቂያ ሚኒስትር ሳሌባን ዩሱፍ አሊ ኮሬ በሀርጌሳ በሰጡት መግለጫ ÷ ቢቢሲ ለ30 ዓመታት ራሷን ችላ ለቆመችው ዴሞክራሲያዊ ግዛት ዕውቅና አልሰጠም ብለዋል።
ከዛሬው ዕለት ጀምሮም ቢቢሲ በግዛቷ የሚሠራቸውን ሥራዎች እንዲያቆም መወሰኑን ነው የገለጹት፡፡
ሚኒስትሩ ÷ ጣቢያው የሚያሰራጫቸው መረጃዎች ለሶማሊላንድ ሕዝብ ጆሮ እንደማይመጥኑም አስገንዝበዋል፡፡
በፈረንጆቹ 1991 በሶማሊያ ተቀስቅሶ በነበረው የእርስ በርስ ጦርነት ሶማሊላንድ ከሶማሊያ ነጻ መሆኗን እንዳወጀች ዘ ኢስት አፍሪካን በዘገባው አስታውሷል ፡፡
ስለ እገዳው ከቢቢሲ የተሰጠ አስተያየት አለመኖሩ ተመላክቷል፡፡
ከእሲያ ሀገራት ውስጥም ቻይና ባሳለፍነው ዓመት ቢቢሲን ከስራ ማገዷ ይታወሳል፡፡
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!